Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ከጭፍን ተከታይነት መጠንቀቅ


ከጭፍን ተከታይነት መጠንቀቅ

ከሱንና ሰዎች አበይት መገለጫዎች ውስጥ አንዱ የፈለገ ቢገንኑ ለዑለማዎች ጭፍን ወገንተኛ አለመሆን ነው፡፡ የፈለገ ብንወደው ማንም ቢሆን የተናገረው ሁሉ ልክ አይሆንም፡፡ ስለሆነም ለማንም ጭፍን ወገንተኛ ልንሆን አይገባም፡፡ ዑለማዎቻችንን ስለወደድናቸው ብቻ ንግግራቸውን እንደወረደ አንወስድም፡፡ ይህንን በተግባር ያስተማሩን እራሳቸው ዑለማዎቹ ናቸው፡፡ ለአብነት ያክል የአራቱን አኢማዎች ንግግሮች እዚህ ላይ ላስፍር፡-

[ሀ] አቡ ሐኒፋ ረሒመሁላህ፡-

1. “አንድ ሐዲሥ ትክክለኛ ከሆነ መዝሀቤ እሱ ነው፡፡”
2. “ከየት እንደወሰድነው ካላወቀ ለማንም አቋማችንን ሊወስድ አይፈቀድለትም፡፡”
3. “ማስረጃዬን ያላወቀ ሰው በኔ ንግግር ፈትዋ ሊሰጥ ሐራም ነው፡፡”
4. “እኛ ሰዎች ነን፡፡ አንድ ንግግር ዛሬ እንናገርና ነገ ከሱ እንመለሳለን፡፡”
5. “የላቀውን አላህ መፅሐፍና የመልእክተኛውንﷺ ንግግር የሚፃረር ንግግር ከተናገርኩኝ የኔን ንግግር ተውት፡፡”

[ለ] ኢማሙ ማሊክ ረሒመሁላህ፡-

1. “እኔ ሰው ነኝ፡፡ እስታለሁ፣ አገኛለሁ፡፡ ስለዚህ እይታየን ተመልከቱ፡፡ ቁርኣንና ሱንና ጋር የገጠመውን በሙሉ ያዙት፡፡ ቁርኣንና ሱንና ጋር ያልገጠመውን ተውት፡፡”
2. “ከነብዩ ﷺ በስተቀር ንግግሩ የሚያዝለት ወይም የሚመለስበት ያልሆነ አንድም የለም፡፡”
3. “ከነብዩ ﷺ በኋላ ከንግግሩ የሚያዝና የሚተው ያልሆነ አንድም የለም፡፡ ነብዩ ﷺ ሲቀሩ፡፡"

[ሐ] ኢማሙ አሽሻፊዒይ ረሒመሁላህ እንዲህ ብለዋል፡-

1. “አንድ የነብዩﷺ ሱንና የተገለፀለት ሰው ለማንም ንግግር ሲል እሷን (ሱንናዋን) መተው እንደማይፈቀድለት ሙስሊሞች በሙሉ ኢጅማዕ አድርገዋል፡፡”
2. “በኪታቤ ውስጥ ከአላህ መልእክተኛﷺ ሱንና የሚፃረር ነገር ካገኛችሁ የአላህ መልእክተኛንﷺ ሱንና ተከተሉ፡፡ የኔን ንግግር ተውት፡፡”
3. “ሐዲሥ ትክክለኛ (ሶሒሕ) ከሆነ መዝሀቤ እሱ ነው፡፡”
4. “እኔ ከተናገርኩት በተቃራኒ በዘርፉ ምሁራን ዘንድ ከአላህ መልእክተኛﷺ ትክክለኛ ዘገባ የመጣበት ርእስ ሁሉ እኔ በህይወት ሳለሁም ሆነ ሞቼ ከሱ ተመልሻለሁ፡፡”

[መ] ኢማሙ አሕመድ ረሒመሁላህ፡-

1. “የአውዛዒይ አስተያየት (ረእይ)፣ የማሊክም አስተያየት፣ የአቡ ሐኒፋም አስተያየት ሁሉም አስተያየት ነው፣ እኔ ዘንድ፡፡ መረጃ ያለው ከነብዩ ﷺ እና ከሶሐቦቹ ቅሪት ዘንድ ነው፡፡”
2. “ማሊክንም፣ ሻፍዕይንም፣ አውዛይን፣ ሠውርይን በጭፍን አትከተል፡፡ እነሱ ከያዙበት ያዝ፡፡”
እነዚህንና መሰል ወርቃማ ንግግሮችን ከሸይኹል አልባኒ ረሒመሁላህ “ሲፈቱ ሶላት አንነቢይ” ኪታብ መግቢያ አካባቢ ማግኘት ይቻላል፡፡

ወንድሜ ሆይ! እህቴ ሆይ! እኛ ከዚህ ምን እንማራለን? ከማስረጃ ጋር አገናዝበን ሳይሆን የምንወደው ሸይኽ ስለተናገረ ብቻ የምንነፍስበት ጊዜ የለንም? አሁንስ ተመሳሳይ ስህተት ላለመድገም ዝግጁ ነን? ለራሳችን እውነተኛ እንሁን፡፡
ከላይ ያለፉትን ንግግሮች በአንክሮ እናስተውል፡፡ የህይወታችን ቋሚ መመሪያም እናድርጋቸው፡፡ “ማሊክንም፣ ሻፍዕይንም፣ አውዛይን፣ ሠውርይን በጭፍን አትከተል” የሚለውን የኢማሙ አሕመድ ንግግር አስተውለነዋል? እነዚህን የኡማው ከዋክብት በጭፍን መከተል ካልተፈቀደ ከነሱ በእጅጉ የሚያንሱትንስ በጭፍን መከተል ይፈቀዳልን? ጤነኛ ከሆንክ መልሱ አይጠፋህም፡፡ እናም በተመሳሳይ እንበል፡፡
- ኢብኑ ተይሚያንም፣ ኢብኑል ቀይምንም፣ ኢብኑ ከሢርንም፣ ዘሀቢንም፣… በጭፍን አትከተል፡፡
- ሙሐመድ ኢብኑ ዐብዲል ወህሃብንም፣ ዐብዱርረሕማን ኢብኑ ሐሰንንም፣ ዐብዱልለጢፍ ኣሊ ሸይኽን፣ ሰዕዲንም፣ ሙሐመድ ኢብኑ ኢብራሂንም፣… በጭፍን አትከተል፡፡
- ኢብኑ ባዝንም፣ አልባኒንም፣ ኢብኑ ዑሠይሚንንም፣ ሙቅቢልንም፣… በጭፍን አትከተል፡፡
- ፈውዛንንም፣ ዐብዱል ሙሕሲን አልዐባድንም፣ ጃሚንም፣ መድኸሊንም፣… በጭፍን አትከተል፡፡
- በሰፈርህ፣ በአካባቢህ፣ በሃገርህ ያሉ መሻይኾችንም፣ ተማሪዎችንም የፈለገ ብትወዳቸው በጭፍን አትከተል፡፡ የሐቅ መለኪያ ሚዛንም አታድርጋቸው፡፡ ማንም ይሁን ማን፡፡
እዚህ ላይ ይህ ፅሑፍ ዑለማን ከማክበርና ትንታኔያቸውን ከመጠቀም ጋር የሚፃረር የሚመስለው ካለ የፅሑፉን መልእክት ፈፅሞ አልተረዳም፡፡ የዚህ ፅሑፍ አላማ ግለሰቦችን የሐቅ መለኪያ በማድረግ ሊከሰት ከሚችል ፈተና መጠንቀቅ እንደሚገባ ማሳሰብ ብቻ ነው፡፡ እንጂ የቁርኣንና የሐዲሥን ማብራሪያ የምንወስደው ከዑለማዎች እንደሆነ የሚታወቅ ነው፡፡ ሆኖም ግን የአንዱ ዐሊም ትንታኔ ከሌላው የሚፃረርበት አጋጣሚ ብዙ ነው፡፡ ይህም ማናቸውንም በጭፍን ልንከተል እንደማይገባ የሚያሳይ ነው፡፡ ዛሬ ግን ታላላቅ መሻይኾችን ቀርቶ በአካባቢያቸው የሚገኙ ዝቅ ያሉ አስተማሪዎችን ጭምር በጭፍን በመከተል የወደዱትን የሚወዱ፣ የጠሉትን የሚጠሉ፣ የነኩትን የሚነኩ፣ የፈቀዱትን የሚፈቅዱ፣ የከለከሉትን የሚከለክሉ፣ ያስጠነቀቁትን የሚያስጠነቅቁ ብዙ ናቸው፡፡ የሚከተሏቸው ሰዎች በሆነ ምክንያት አቋም ሲቀይሩም ያለምንም ማገናዘብ ሰልፋቸውን በመቀየር ዥዋዥዌ ይጫወታሉ፡፡ ይሄ ፈፅሞ ሊሆን አይገባም፡፡ አላህ ማስተዋሉን ያድለን፡፡

(ኢብኑ ሙነወር፣ ሐምሌ 07/2010)

Post a Comment

0 Comments