Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

"አላህ የት ነው?" የቁርአን ተፍሲር ምሁራንስ ምን አሉ?

"አላህ የት ነው?" የቁርአን ተፍሲር ምሁራንስ ምን አሉ?
ውዝግቡ ከተነሳ በኋላ የችግሩ ሰለባ የሆኑትን ሳይሆን በዚህ ጉዳይ ላይ ንትርክ ከመነሳቱ ቀደም ብሎ የነበሩና እነሱን በመልካም የተከተሉ ሙፈሲሮች በዚህ ጉዳይ ላይ የነበራቸውን አቋም አላህ ከዐርሹ በላይ እንደሆነ ማፅደቅ ነው፡፡ በዚህ ረገድ የተላለፉ ማስረጃዎች ማዳረስ ስለማይቻል እንዲሁ ለምሳሌ ያክል ብቻ ጥቂት እጠቅሳለሁ፡፡
➊. ዐብዱላህ ኢብኒ ዐባስ ረዲየላሁ ዐንሁ፡ ለዓኢሻ እንዲህ ብለዋቸዋል፡ "ከአላህ መልእክተኛ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ባለቤቶች ሁሉ ይበልጥ የተወደድሽ ነበርሽ፡፡ እሳቸው ደግሞ ጥሩን እንጂ የሚወዱ አልነበሩም፡፡ አላህም ከሰባት ሰማያት በላይ ሆኖ  ንፅህናሽን አውርዷል፡፡" (ሙኽተሰሩልዑሉው፡ 130)
➋. ዐብዱላህ ኢብኒ መስዑድ ረዲየላሁ ዐንሁ፦ "ዐርሹ ከውሃው በላይ ነው፡፡  አላህ ደግሞ ከዐርሹ በላይ_ነው፡፡ ሆኖም ከስራዎቻችሁ ምኑም አይሰወረውም፡፡" ቡኻሪ ዘግበውታል፡፡ (ኸልቁ አፍዒሊልዒባድ፡ 43) (ሙኽተሰሩልዑሉው፡ 103-104)
➌.ሙጃሂድ ረሒመሁላህ፦ "ኢስተዋ" የሚለውን ቃል "ከፍ አለ" ብለው እንደፈሰሩት አልኢማም አልቡኻሪ ዘግበዋል፡፡ (ፈትሑልባሪ፡ 18/429) {ወቀረብናሁ ነጂያህ} የሚለውን ሲያብራሩም እንዲህ ብለዋል፡ " በሰባተኛው ሰማይና በዐርሽ  መካከል ሰባ ሺህ መጋረጃ አለ፡፡  ሙሳን እያቀረባቸው ቀጠለ፣  በርሳቸውና በአላህ መካከል_አንድ  መጋረጃ እስከሚቀር_ድረስ፡፡" (ሙኽተሶሩልዑሉው፡ 132)
➍.ቀታዳህ ረሒመሁላህ (ታቢዒይ ናቸው) እንዲህ ይላሉ፦ "የኢስራኢል ልጆች እንዲህ አሉ፦ ጌታችን ሆይ! አንተ በሰማይ ነህ፡፡ እኛ ደግሞ ምድር ላይ፡፡ ውዴታህን ከቁጣህ እንዴት (ለይተን) እናውቃለን?" እሱም አላቸው፡ "ከናንተ ከወደድኩኝ ምርጦቻችሁን በናንተ ላይ እሾማለሁ፡፡ ከተቆጣሁኝ ግን መጥፎዎቻችሁን በናንተ ላይ እሾምባችኋለሁ፡፡" (ሙኽተሶሩልዑሉው፡ 130)
➎. አድዶሓክ ረሒመሁላህ፦ {ሶስት ሰዎች ሹክሹክታ ላይ አይሆኑም አራተኛቸው አላህ ቢሆን እንጂ} በሚለው የአላህ ንግግር ላይ "እሱ ከዐርሹ ላይ_ነው፡፡ እውቀቱ ግን ከነርሱ ጋር ነው" ብለዋል፡፡ (ሙኽተሶሩልዑሉው፡ 138)
➏. ሙቃቲል ኢብኑ ሐያን (150 ሂ.)፦ {ሶስት ሰዎች ሹክሹክታ ላይ አይሆኑም አራተኛቸው አላህ ቢሆን እንጂ} በሚለው የአላህ ንግግር ስር " እሱ ከዐርሹ_ላይ_ነው፡፡ እውቀቱ ግን ከነርሱ ጋር ነው" ብለዋል፡፡ (ሙኽተሶሩልዑሉው፡ 138)
➐. አቡ ኢስሓቅ አሥሠዕለቢ ረሒመሁላህ፦ የታወቁ የቁርአን ተንታኝ ነበሩ፡፡ {አርረሕማን ከዐርሹ በላይ ሆነ} በሚለው ላይ "እሱ እራሱን እንደገለፀው ከዐርሹ በላይ ነው" የሚለውን የአውዛዒን ረሒመሁላህ ንግግር አስፍረዋል፡፡ (ሙኽተሶሩልዑሉው፡ 138)
➑. አልሓፊዝ ቢሽር ኢብኑ ዑመር አዝዘህራኒይ ረሒመሁላህ (270 ሂ.)፦ "{አርረሕማን ዐለልዐርሺ ኢስተዋ} የሚለውን ብዙ ሙፈሲሮች (የቁርአን ተንታኞች) "ከዐርሹ በላይ ነው" ሲሉት ሰምቻለሁ" ብለዋል፡፡ (ሙኽተሶሩልዑሉው፡ 160)
➒. ኢብኑ ጀሪር አጥጦበሪ ረሒመሁላህ (310 ሂ.)፦ "አንድ ሰው ጌታው በሰማያትም፣ በምድርም፣ በመካከላቸውም እንዲሁም ከአፈር በታችም ያለው ሁሉ ባለቤት የሆነው ያ ከዐርሹ በላይ የሆነው እንደሆነ ማወቁ በቂው ነው፡፡ ይህን የተሻገረ በርግጥም አፈረ፣ ከሰረ፡፡ ጠመመ፣ ጠፋ!!!" ይላሉ፡፡ (ሶሪሑስሱናህ፡ 26-27)
➓. አልኢማም አልቁርጡቢ ረሒመሁላህ (671 ሂ.) ፈር የለቀቁ ሰዎችን አቋም ካሰፈሩ በኋላ "የመጀመሪያዎቹ ሰለፎች አላህ ይውደድላቸውና ወደላይ አቅጣጫ መሆኑን አላስተባበሉም፡፡ እንዲህ ብለውም አልተናገሩም፡፡ ይልቁንም እነሱ ቁርአኑ እንደተናገረው መልእክተኞችም እንዳወሩት ባጠቃላይ  ከፍ ላለው አላህ የላይ አቅጣጫን አፅድቀዋል፡፡ አንድም እሱ በሐቂቃ  ከዐርሹ በላይ እንደሆነ የተቃወመ የለም፡፡ ያላወቁት ከዐርሹ በላይ የመሆኑን እንዴትነት ነው፡፡" (ተፍሲሩልቁርጡቢ፡ 7/220)
➊➊. ኢብኑ ከሢር (748 ሂ.) ረሒመሁላህ፦ "{አርረሕማን ዐለልዐርሺ ኢስተዋ} የሚለውን በተመለከተ በዚህ ላይ ሰዎች እጅግ በርካታ ነገር ነው ያላቸው፡፡ ይሄ ግን በዝርዝር የምናነሳበት ቦታ አይደለም፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ የምንጓዘው የመልካም ቀደምቶችን መንገድ ነው፡፡ የነ ማሊክ፣ አልአውዛዒይ፣ አሥመውሪይ፣ አልለይሥ ኢብኑ ሰዕድ፣ አሽሻፊዒይ፣ አሕመድ፣ ኢስሓቅ ኢብኑ ራሀወይህ እና ሌሎችም ከጥንት እስከ ዛሬ ያሉ የሙስሊም ምሁራንን (መንገድ ነው የምንጓዘው፡፡) እሱም ያለ ሁኔታ፣ ያለ ማመሳሰል እና ያለ ማራቆት እንደመጣ ማፅደቅ ነው፡፡ ከአመሳሳዮች ህሊና ውስጥ ቀድሞ የሚመጣው ነገር ከአላህ የተነሳ ነው፡፡ ምክንያቱም አላህ ከፍጡሩ ምንም የሚመስለው የለምና፡፡ {የሚመስለው ምንም ነገር የለም! እሱም ሰሚው ተመልካቹ ነው} ይልቁንም ጉዳዩ እንደ ኑዐይም ኢብኑ ሐማድ አልኹዛዒይ (የቡኻሪ ሸይኽ) ያሉ ታላላቅ መሪዎች እንዳሉት 'አላህን ከፍጡሩ ጋር ያመሳሰለ በርግጥም ከኢስላም ወጥቷል፡፡ አላህ እራሱን የገለፀበትን የካደ በርግጥም ከኢስላም ወጥቷል፡፡ አላህ እራሱን ከገለፀበትና መልእክተኛው እሱን ከገለፁበት ውስጥ ማመሳሰል የለም፡፡' ስለዚህ ግልፅ የሆኑ አንቀፆች እና ትክክለኛ ሐዲሦች የመጡበትን ለላቀው አላህ ለልቅናው በሚገባ መልኩ ያፀደቀ እና ከአላህም ጉደለቶችን ያጠራ በርግጥም ቅኑን መንገድ ነው እየተጓዘ ያለው፡፡" (ኢብኑ ከሢር፡ 2/912)


#Written by አቡ ቢላል ሁሴን (ተውሒድ የሁለት ሀገር የስኬት ቁልፍ ገጽ 101-103)

Post a Comment

0 Comments