Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ሸውካኒ እና መውሊድ (ወሳኝ ነጥቦች የተዳሰሱበት)


ሸውካኒ እና መውሊድ (ወሳኝ ነጥቦች የተዳሰሱበት)
~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~
ሙሐመድ ኢብኑ ዐሊ አሽሸውካኒ በ1250 ሂ. የሞቱ ታላቅ የመናዊ ዓሊም ናቸው፡፡ በሰፊው የሚታወቁ ስለሆኑ እሳቸውን በማስተዋወቅ ፅሑፌን ማስረዘም አልሻም፡፡ ሸውካኒ መውሊድ ላይ እጅግ የሰላ ትችት ሰንዝረዋል፡፡ ዛሬ በተደጋጋሚ ከምንሰማቸው መውሊድ ተኮር ጥያቄዎች ውስጥ የተወሰኑትን በመምዘዝ በሸውካኒ ንግግር ምላሽ ለመስጠት ሞክሬያለሁ፡፡ ሙሉ ንግግራቸውን መመልከት የፈለገ ሰው “አልፈትሑ ረባኒ ሚን ፈታወል ኢማሚ ሸውካኒ” በተሰኘው የፈትዋ መድብላቸው ውስጥ ሁለተኛውን ጥራዝ ከገፅ 1087-1101 ድረስ መመልከት ይችላል፡፡ ፅሑፉ ስለ ረዘመ ዐረብኛውን ማካተት አልቻልኩም፡፡
1. መውሊድ የሸሪዐ መነሻ አለውን?
ሸውካኒ፡- “እስካሁን ድረስ ከቁርኣንም፣ ከሱናም፣ ከኢጅማዕም፣ ከቂያስም (ንፅፅራዊ ምልከታም) መሰረት እንዳለው የሚያመላክት መረጃ አላገኘሁለትም፡፡” [ገፅ፡ 2/1087]
2. መውሊድን ሰለፎች ያውቁታል?
ሸውካኒ፡- “እንዲያውም ከዘመናት ሁሉ ምርጡ በሆነው (የሶሐቦች) ዘመንም፣ ከነሱ ቀጥሎ በነበሩትም፣ ቀጥሎ በነበሩትም (ዘመን) እንዳልነበር ሙስሊሞች ወጥ አቋም ይዘዋል (ኢጅማዕ አድርገዋል፡፡)” [ገፅ፡ 2/1087]
3. ቢድዐ በመሆኑ ላይ ልዩነት አለ?
ሸውካኒ፡- “ቢድዐ በመሆኑ ላይ ከሙስሊሞች አንድ እንኳን የተቃወመ የለም፡፡” [ገፅ፡ 2/1088] “ይሄ ነገር ቢድዐ በመሆኑ ላይ ከሁሉም ሙስሊሞች ኢጅማዕ እንዳለበት አረጋግጠንልሃል፡፡” [ገፅ፡ 2/1091]
4. መውሊድን በሚደግፉ መሻይኾች ማስፈራራት ያዋጣል?
ሸውካኒ፡- “በምርጡ ነብይ ﷺ የማያሻማ ምስክርነት ቢድዐ ሁሉ ጥመት እንደሆነ ተነግሮ ሳለ የመውሊድን ቢድዐ መሆን ካመነ በኋላ ይፈቀዳል የሚል ሰው የተናገረው ከንፁሁ ሸሪዐ ጋር የሚፃረር ንግግር ነው፡፡ ያለ አንድ ተጨባጭ እውቀታዊ መነሻ ቢድዐን ወደተለያዩ ክፍሎች ለከፈለ ሰው በጭፍን ከመከተል ያለፈ ነገርም የለውም፡፡ የትኛውንም አቋም ይቻላል የሚልን ሰው ይህንን ቢድዐ በተለየ የሚመለከት ማስረጃ ካቀረበ በኋላ እንጂ አንቀበለውም፡፡ … እንጂ ‘እከሌ እንዲህ አለ’፣ ‘እከሌ እንዲህ አይነት ኪታብ አዘጋጅቷል’ የሚል ባዶ ንግግር ፋይዳ የለውም፡፡ ሐቅ ከየትኛውም አካል ይበልጣልና፡፡” [ገፅ፡ 2/1088 - 1089]
“ከነሱ (ከፈቃጆቹ) ውስጥ ቢድዐነቱን አምኖ መጥፎ ነገር ካልተቆራኘው በሚል መስፈርት የፈቀደው አለ፡፡ ምንም ማስረጃ ግን አላመጣም፡፡” [ገፅ፡ 2/1094]
ኢብኑ ሐጀር እንዳደረገው የዓሹራን ፆም ማስረጃ ማድረግ፣ ወይም ሲዩጢ እንዳደረገው ከነብይነት በኋላ ለራሳቸው ዐቂቃ ማውጣታቸውን መመርኮዝ ቢድዐን የማፅናት ፍቅር እንዲህ አይነት ነገር ላይ እንደሚጥል ከሚያሳዩ አስገራሚ ነገሮች ውስጥ ነው፡፡ [ገፅ፡ 1095]
5. መውሊድ የብዙሃን ሙስሊሞች ድጋፍ ነበረውን?
ሸውካኒ፡- “በሰዎች ንግግሮች ላይ የምንመረኮዝ ከሆንና የእንቶ ፈንቶ ጅራቶችን የምንጨብጥ ከሆንን መታወቅ ያለበት ነገር ቢኖር ‘ይፈቀዳል’ ባዮቹ ከሙስሊሞች በአቋም ያፈነገጡ ናቸው፡፡ …” [ገፅ፡ 2/1087-1089]
“ሲጨመቅ የመውሊድ ፈቃጆች ከከልካዮቹ አንፃር ሲታዩ ጥቂቶች ናቸው፡፡ ለዚያውም እነሱም ቢሆኑ ምግብ ለማብላትና ለዚክር ካልሆነ በስተቀር እንደማይቻል ተስማምተዋል፡፡” [ገፅ፡ 1095–1099]
(አስተውሉ! ይህ እንግዲህ በሸውካኒ ዘመን ነው፡፡ የሞቱት በ1250 ሂ. ሲሆን ሁለት መቶ አመት ሊሞላቸው ጥቂት ነው የቀራቸው፡፡ አሕባሽ ደፋር ነውና የዛሬን የመውሊድ ጨፋሪዎች በመመልከት ሸውካኒን “ውሸታም ነው” እንዳይሉ እሰጋለሁ፡፡)
6. መውሊድ እንዴት ተስፋፋ?
ሸውካኒ፡- “ግና ቢድዐን በማፅናትም ሆነ በማውደም ላይ ለንጉሳን ተፅእኖ አላቸው፡፡ ይህንን ቢድዐ (በሱኒው ዓለም ውስጥ) የፈጠረው ያ ንግስ (ሙዞፈር) ሲሆን ኢብኑ ዲሕያ ደግሞ ‘አትተንዊር ፊ መውሊዲል በሺር አንነዚር’ የተሰኘ ኪታብ በማዘጋጀት አግዞታል፡፡ ሰውየው በዘገባ እውቀት ላይ የጠለቀ ከመሆኑም ጋር በዚህ ኪታቡ ግን ግልፅ ማስረጃ አላቀረበም፡፡ ለዚህ ስራው - ኢብኑ ኸሊካን እንዳወሱት - አንድ ሺህ ዲናር በንጉሱ መሸለሙ ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ የዱንያ ፍቅር ከዚህም በላይ ያደርሳል፡፡” [ገፅ፡ 2/1091]
“የቢድዐ ስርጭት ከእሳት ስርጭት የፈጠነ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ መውሊድ፡፡ ምክንያቱም የመሃይማን ነፍሶች ጥግ የደረሰ መናፈቅን ይናፍቁታልና፡፡ በተለይ ደግሞ ከምሁራን፣ ከክቡራንና መሪዎች በርከት ያለ ሰው ከተካፈለበት በኋላ ይሄ ቢድዐ ወሳኝ ከሆኑ ሱናዎች ይመስላቸዋል፡፡ … እንደ መውሊድና አምሳያዎቹ ያሉ ለሐራም ነገሮች የሚያመቻቹ የጥፋት መዳረሻዎች መሃይሞች ፈጥነው እንደሚገቡባቸው አያጠራጥርም፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ በዒልም፣ በክብርና በስልጣን ዝና ያለው ሰው መካፈል ሲታከልበት ሐራም ነገሮችን እንደ ፈጣሪ ትእዛዛት ሲፈፅሙ፣ በድንቁርናና በጥመት ሸለቆች ውስጥ ገብተው ሲዘባርቁ፣ “የተከበሩ እከሌ፣ እከሌ፣ እከሌ፣… ተገኝተዋል” እያሉ ከተቃውሞ ሲያመልጡ የባሰ ይሆናል፡፡
መሃይሙ ህዝብ ይቅርና አንዱ በዒልም ፍለጋ ላይ ገኖ የወጣ ሰው አንዳንድ የኢጅቲሃድ እውቀቶችን ለመማር ከፊቴ ተቀምጦ ነበር፡፡ በዚህ ወር ከተከናወኑ መውሊዶች ውስጥ በአንዱ አዳር ላይ እንደተካፈለ ሲነግረኝ ተቃወምኩት፡፡ አንገሸገሸኝ፡፡ በዚህን ጊዜ ‘ሰዪዲ እከሌ፣ እከሌ፣ እከሌ፣… ተካፍለዋልኮ’ አለኝ፡፡ በነዚህ ታዋቂ ሰዎች ፊት የነበረውን አፈፃፀም ስጠይቀው እንዲህ አለኝ፡-
‘እነዚያ ታዋቂ ሰዎች እየዘፈኑና እያዳመጡ መንዙማውን አንድ ሱቂ አነበበ፡፡ ከዚያም አንዱ ልክ ከእስር የተነሳ ይመስል አፈፍ ብሎ ተነስቶ “መርሐባ ያ ኑረ ዐይኒ፣ መርሐባ” (እንኳን መጣህ ያይኔ ብርሃን እንኳን መጣህ!) ሲል ታዳሚው በመላ ታዋቂዎቹን ጨምሮ ተከትለውት ቆሙ፡፡ እነሱ በዚህ ሁኔታ ላይ እያሉ ቆሞ ማጓራት ያዘ፡፡ አንዱ ታዳሚ ደክሞት ቢቀመጥ ከታዋቂዎቹ ውስጥ አንዱ ንዴቱ ከፊቱ ላይ እየታየ ተነስ ጨዋታኮ አይደለም! ብሎ ጮኸበት፡፡ ቃል በቃል!ት የአላህ መልእክተኛ ﷺ በዚያች ሰዓት ከነሱ ዘንድ እንደደረሱ ጭራሽ አይጠራጠሩም፡፡ ከዚያም ተጨባበጡ፡፡ ከተራው ሰዎች ከፊሎቹ በእጆቻቸው ሽቶ በመያዝ በፍጥነት ቀቡ፣ ተቀቡ፡፡ ልክ የሳቸውን ﷺ መገኘት ለመጠቀም፡፡’
ኢንና ሊላሂ ወኢንና ኢለይሂ ራጂዑን! የዲን ክብር የት ገባ?! ይህም ከጠፋ አይናፋርነት፣ ግብረ ገብነት፣ ህሊና የት ገባ?” [ገፅ፡ 2/1089-91]
7. መውሊድን የነብዩ ﷺ ቤተሰቦች ይደግፉታል?
መውሊድን የሚያከብሩ ሰዎች “ከኛ በላይ ነብዩን ﷺ የሚወድ ላሳር!” የሚሉ ናቸው፡፡ እውነት ለመናገር የነብዩ ﷺ ዘሮች ሙእሚኖች ከሆኑ ለነብዩ ﷺ ያላቸው ፍቅር ልዩ ነው፡፡ መውሊዱ የፍቅር መገለጫ ቢሆን ኖሮ ከማንም ቀድመው ባከበሩት ነበር፡፡ ግን ከነሱ የተገኘው መውሊድን ማክበር፣ ማስከበር፣ ለሱ ሽንጥን ገትሮ መሟገት ነውን?
ሸውካኒ፡- “ከነብዩ ﷺ ንፁሕ ቤተሰብም ይሁን ከተከታዮቻቸው ይህ ነገር እንደሚፈቀድ የተናገረ አንድም ፊደል አላገኘንም፡፡ እንዲያውም ይህቺ ቢድዐ ከተከሰተች ጀምሮ ወደ ጥፋቶች ከሚያሻግሩ አስቀያሚ መዳረሻዎች አንዷ እንደሆነች ንግግሮቻቸው ከሞላ ጎደል ተስማምተዋል፡፡” [ገፅ፡ 1089]
“ከነብዩ ﷺ ቤተሰቦች እና ከተከታዮቻቸው ውስጥ ‘መውሊድ ይፈቀዳል’ ያለ አንድ እንኳን እንደሌለ ከተገለፀልህ ከነሱ ውጭ ያሉትን አቋም ልታውቅ ከፈለግክ ከሁሉም ሙስሊሞች ዘንድ ቢድዐ በመሆኑ ላይ ኢጅማዕ እንዳለ አረጋግጠንልሃል እንላለን፡፡” [ገፅ፡ 1091]
8. መውሊድ ውስጥ ሺርክ ወይም ሌላ ጥፋቶች ከሌሉበትስ ይፈቀዳል?
ሸውካኒ፡- “ ‘መውሊዱ ላይ ለምግብ መሰባሰብና ዚክር ብቻ ከሆነ ይፈቀዳል፣ አብረውት የሚያጅቡት ነገሮች ክልክል መሆናቸው ክልክልነቱን አያሲዝም’ የሚሉ ሰዎች ማመሀኛ ፉርሽነቱ ከዚህ ላይ ግልፅ ይሆንልሀል፡፡ ምክንያቱም እኛ እራስህ እንዳመንከው መውሊድ ቢድዐ ከመሆኑ ጋር በልምድ ከብዙ መጥፎ ነገሮች ጋር የተቆራኘና ለብዙ ጥፋቶች መዳረሻ ሆኗል እንላለንና፡፡ ደግሞም ከምግብና ከዚክር ውጭ ያሉ ነገሮችን የማያካትቱ መውሊዶችን ማግኘት ከቀይ ክብሪት የበለጠ ፈታኝ ነው፡፡” [ገፅ፡ 2/1090-1091]
“የመውሊድ ፈቃጆች ከከልካዮቹ ጋር ሲነፃፀሩ ጥቂቶች ከመሆናቸው ጋር ለምግብና ለዚክር ብቻ በሚል መስፈርት ካልሆነ በስተቀር እንደማይቻል ተስማምተዋል፡፡ ለብዙ ጥፋቶች መዳረሻ እንደሆነ ደግሞ ይሄው አሳውቀንሃል፡፡ ይህን ከግምት በማስገባት ላይ አንድም አይፃረርም፡፡ ዛሬ የሚከሰተው የዚህ አይነቱ (ጥፋቱ የበዛበት) መውሊድ ግን በወጥ ስምምነት የተከለከለ ነው፡፡” [ገፅ፡ 2/1098-1099]
“ወደ ጥፋት የሚያደርሱ መንገዶችን መዝጋትና ወደማይፈቀድ ነገር መንጠላጠያ ገመዶችን መቁረጥ ብዙሃን ምሁራን እርግጠኛ ከሆኑባቸው ወሳኝ ሸሪዐዊ መርሆዎች ውስጥ ነው፡፡ አንተ እራስህ እንጥፍጣፊ ሚዛናዊነት ቀርቶህ ከሆነ ይህንን ሐቅ አትክድም፡፡” [ገፅ፡ 2/1091]
9. መውሊድ የልዩነት መንስኤ ነውን?
ሸውካኒ፡- “ደግሞም ይሄ መውሊድ ከተከሰተ በኋላ ውዝግቡ ተጧጡፏል፡፡ በዚህም ላይ የሚፃፉት ኪታቦች ከከልካዩም ከፈቃጁም በዝተዋል፡፡” [ገፅ፡ 2/1091]
10. መውሊድ ውስጥ አስቀያሚ ጥፋቶች ከኖሩበትስ?
ሸውካኒ፡- “ሲጨመቅ የመውሊድ ፈቃጆች ከከልካዮቹ አንፃር ሲታዩ ጥቂቶች ናቸው፡፡ ለዚያውም እነሱም ቢሆኑ ምግብ ለማብላትና ለዚክር ካልሆነ በስተቀር እንደማይቻል ተስማምተዋል፡፡ ለጥፋቶች መዳረሻ እንደሆነ ደግሞ በርግጥም አሳውቀንሃል፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ አንድም የሚወዛገብ የለም፡፡ የዚህ አይነቱ ዛሬ እየተከሰተ ያለው መውሊድ በዑለማእ ስምምነት ክልክል ነው፡፡ ርእሱ የፈቃጆቹን ንግግሮች እያቀረቡ ዘለግ ባለ መልኩ መመለስ የሚጠይቅ ቢሆንም ለጊዜው እዚህ ላይ ይበቃናል፡፡” ከዚያም በሙታን ላይ የሚፈፀመውን ሺርክና የጣኦት አምልኮ ጠቅሰው በጥብቅ ከኮነኑ በኋላ “እኛ ማስጠንቀቅና ማድረስ እንጂ ሌላ አቅም የለንም፡፡ ይህንን ይሄው አድርገናል፡፡ አላህ ሆይ! ለዲንህ ተቆጣ! ከነዚህ ቀብር አምላኪ ሸይጧኖች ቆሻሻም አፅዳው፡፡ ከነዚህ የጠንካራውን እምነት ንፅህና ካጠለሹ ቆሻሻዎችም አሳርፈን፡፡” [ገፅ፡ 1095–1101]

ከ “መውሊድ፤ ታሪክ፣ ግድፈት፣ እርምት” መፅሐፍ ተነካክቶ የተወሰደ

Post a Comment

0 Comments