Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

መውሊድ የማያከብር ሰው የሙሐመድ ﷺ ጠላት ከሆነ፣ ገና የማያከብር ሰው የዒሳ ጠላት ነው!


መውሊድ የማያከብር ሰው የሙሐመድ ﷺ ጠላት ከሆነ፣ ገና የማያከብር ሰው የዒሳ ጠላት ነው!
~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~
መውሊድ ቀደምት የኢስላም ትውልዶች ዘንድ የማይታወቅ መጤ ፈጠራ መሆኑን እራሳቸው የመውሊድ አክባሪ የሆኑ አካላት የመሰከሩትን አሳልፌያለሁ። እነዚሁ አካላት መውሊድ ከክርስቲያኖቹ ገና ተኮርጆ በፉክክር እንደሚከበር የተናገሩቱን ደግሞ እናያለን። ዘግይተው የመጡ አንዳንድ የነጋባቸው ሱፍዮች ግን “መውሊድ በሀይማኖታችን መረጃዎች መሰረት የተፈቀደ በመሆኑ ላይ ከተግባባን ከክርስቲያን ወይም ከሂንዱ እምነት ጋር ባጋጣሚ ተመሳስሎ ቢገኝ ችግር የለውም” ይላሉ። በሀይማኖታችን መሰረት ቢኖረውማ እነ ኢብኑ ሐጀር “የመውሊድ ተግባር መሰረቱ ቢድዐ ነው። በሶስቱ ክፍለ ዘመናት ከነበሩት መልካም ቀደምቶች ከአንድም አልተላለፈም” አይሉም ነበር።
እያከበሩ ያሉት ሌላ መልክ ያለው ገና ነው። chrismas ማለት ልደት ማለት ነው። ልደት ማለት ደግሞ በዐረብኛው መውሊድ ማለት ነው። ስለዚህ የሚከበረው ስብእና እንጂ የተለየው የሚያከብሩት ገናን ነው። የክርስቲያኖች ገና = የሱፍዮች መውሊድ!! የክርስቲያኖች መውሊድ = የሱፍዮች ገና!!
እንዲያውም መውሊድን የሚያከብሩት ከክርስቲያኖች ጋር ለመፎካከር ብለው ነው። የፉክክር ዒባዳ!! ይህንን ሐቅ በኪታብ ሳይቀር ያሰፈሩት አሉ። ለምሳሌ፡-
1. ሰኻዊ ምን እንደሚሉ ተመልከቱ፡- “ባለ መስቀሎቹ (ክርስቲያኖች) የነብያቸውን ልደት ትልቁ ዒዳቸው አድርገው የሚይዙ ከሆነ ሙስሊሞችም (ነብያቸውን) በማክበርና በማላቅ ይበልጥ የተገቡ ናቸው።” [አትቲብሩል መስቡክ፡ 14]
2. ከጀዘሪም ቃል በቃል ተላልፏል።
3. መውሊድን ለምዕራቡ ዐረቢያ ያስተዋወቁት አቡል ዐባስ አልአዘፊም፡- በክርስቲያን በዓላት ላይ የሚሳተፉ ወጣቶችን ለመመለስ ሲሉ እንደጀመሩት በግልፅ ተናግረዋል።
4. የአሕባሾቹ መሪ ዐብዱላህ አልሀረሪም እንዲሁ ንጉስ ሙዞፈር መውሊድን የጀመረው ክርስቲያኖች የመሲሕ ልደትን በዓል ሲያከብሩ ተመልክቶ ነው። በዚህም ሳቢያ ሰይዳችንን ሙሐመድን ﷺ ስላወጣልን አላህን ለማመስገን ሲል መውሊድን ጀመረ ይለናል። [ኢዝሃሩል ዐቂደቲ አስሱንያህ፡ 240]
የመውሊድ ደጋፊዎች ምን ያክል በፉክክር እንደተለከፉ ተመልከቱ። ነብዩ ﷺ “ከሆኑ ሰዎች ጋር የተመሳሰለ ከነሱው ነው” ማለታቸው ይታወስ። [ኢርዋኡል ገሊል፡ 1269] እንዲያውም “ከናንተ በፊት የነበሩ ሰዎችን ፈለጎች ስንዝር በስንዝር ክንድ በክንድ ትከተላላችሁ። የአርጃኖ ጉድጓድ ቢገቡ እንኳን በርግጥም ትገቡታላችሁ!” ሲሉ “አይሁድና ክርስቲያኖችን ነው (ትከተላላችሁ) የምትለን?” ብለው ቦጠይቁ “ታዲያ ማንን ነው?!” ነበር ያሉት። [ቡኻሪ፡ 7320]
የተናገሩት በትክክል ተፈፀመ። ለብዙ ጥፋቶች የሚያጋልጠው በዓል ከክርስቲያኖች ተኮርጆ በ "ፋጢሚያ" ሺዐዎች ዳብሮ፣ በሱፍዮች ተሸጋግሮ ብዙሃኑ ሙስሊም ሊዘፈቅበት በቅቷል።
የሚያሳፍረው “ክርስቲያኖቹ የነብያቸውን ልደት እያከበሩ የኛ ነብይ ከማን ያንሳሉ?” የሚሉት ነገር ነው። ሱብሓነላህ! ለመሆኑ ዒሳ የኛ ነብይ አይደሉም እንዴ?! ታዲያ ይሄ ምን የሚሉት አፀያፊ ሎጂክ ነው? ደግሞ ምንም ሳያፍሩ መውሊድን የሚቃወሙ ሙስሊሞችን “የነቢ ጠላቶች ናቸው!” እያሉ ከባድ ክስ ይከሳሉ። የነብዩን ﷺ መውሊድ አለማክበር እሳቸውን መጥላት ከሆነ እናንተም የክርስቲያኖቹን ገና (chrismasን) ባለማክበራችሁ የዒሳ ጠላቶች ናችሁ ማለት ነው። መውሊድን ማክበር ነብዩን ﷺ ማክበር ከሆነ የሌሎቹን ነብያት ልደቶች ስለማታከብሩ ለሌሎች ነብያት በሙሉ ክብር የሌላችሁ የነብያት ጠላቶች ናችሁ ማለት ነው። ከአንደበታችሁ በቀጥታ ባይወጣም አመክኗችሁ የሚሰጠው ይህንን ነው።

እኛ ግን ነብያትን ከነብያት አንለያይም። ጌታችን እንዳዘዘን እንዲህ እንላለን፡-
آمَنَ الرَّسُولُ بِمَا أُنْزِلَ إِلَيْهِ مِنْ رَبِّهِ وَالْمُؤْمِنُونَ كُلٌّ آمَنَ بِاللَّهِ وَمَلَائِكَتِهِ وَكُتُبِهِ وَرُسُلِهِ لَا نُفَرِّقُ بَيْنَ أَحَدٍ مِنْ رُسُلِهِ
“መልእክተኛው ከጌታው ወደርሱ በተወረደው አመነ። አማኞቹም ሁሉም በአላህ፣ በመላእክቱም፣ በመፃህፍቱም፣ በመልእክተኞቹም እንዲሁ አመኑ። ከመልእክተኞቹ በአንድም መካከል አንለይም (ሲሉ አመኑ)።” [አልበቀራህ፡ 285]

ከ “መውሊድ፤ ታሪክ፣ ግድፈት፣ እርምት” መፅሐፍ ተነካክቶ የተወሰደ


Post a Comment

0 Comments