Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ነብዩ ﷺ መቼ ተወለዱ? ሌላ የመውሊድ ራስ ምታት

ነብዩ ﷺ መቼ ተወለዱ? ሌላ የመውሊድ ራስ ምታት
~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~
መውሊድ በኢስላም መሰረት እንደሌለው ከሚያመላክቱ ማስረጃዎች አንዱ ታሪክ ነው። ነብዩ ﷺ በምን ወር ተወለዱ? በስንተኛው ቀን? በስንት አመት? ለነዚህ ጥያቄዎች የሚኖረን መልስ በራሱ የመውሊድን በዓል አላስፈላጊነትና መሰረት-አልባነት ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል።
1. የተወለዱበትን አመት በተመለከተ በዝሆኑ አመት ማለትም የሐበሻው አብረሀ ከዕባን ለማፍረስ በዝሆን የታጀበ ሰራዊት ይዞ የዘመተበት አመት ነው። ይህም እ.ኤ.አ በ 570 ወይም 571 ማለት ነው። በታዋቂዎቹ የሱንና ኪታቦች ውስጥ ይህን የሚያመላክት መረጃ ባይኖርም በኢብኑ ዐባስ ስም በይሀቂ የዘገቡት ግን አለ። ግና ይህም ቢሆን ሰነዱ መጠነኛ ውዝግብ አለበት። “በዝሆኑ አመት በየትኛው ጊዜ?” የሚለው እራሱ የተለያዩ ሀሳቦች ተሰንዝረውበታል። ለምሳሌ ነብዩ ﷺ የተወለዱት፡-
1.1. በዘመቻው እለት ነው የሚል ሰነድ አልባ ዘገባ ከኢብኑ ዐባስ ተዘግቧል።
1.2. ከዝሆኑ ዘመቻ ከወር በኋላ ነው ተብሏል።
1.3. ከዝሆኑ ዘመቻ ከ40 ቀን በኋላ ነው ተብሏል።
1.4. ከዝሆኑ ዘመቻ ከ 50 ቀን በኋላ ነው ተብሏል። [አልኢስቲዓብ፡ 1/30]
የዝሆኑ ዘመቻ ሙሐረም 13 እንደተካሄደ አልኸዋሪዝሚና ሌሎችም የጠቀሱ ሲሆን ሌሎች ደግሞ “የለም ረቢዑል አወል ነው” ይላሉ። የነዚህን ሀሳብ ከግምት ካስገባን 8 የተለያዩ ሃሳቦች ኖሩ ማለት ነው። በሙሐረም ከሆነ አራት፣ በረቢዑል አወል ከሆነ ደግሞ ሌላ አራት። በድምሩ ስምንት።
2. “በምን ወር ተወለዱ?” ለሚለውም ብዙ ሀሳቦች ተነስተዋል።
3.1. በሶፈር ወር ነው ያሉ አሉ።
3.2. በረመዷን ወር ነው ያሉ አሉ። ይሄ ሀሳብ ከታዋቂው የታሪክ ምሁር ዙበይር ኢብኑል በካር (256 ሂ.) እና ከሌሎችም ተላልፏል።
3.3. በሙሐረም ነው ያሉም አሉ። [ጉንየቱ አጥጧሊብ፡ 2/317]
3.4. ረቢዑል አወል ነው ያሉም አሉ። ይሄ ከብዙሃኑ ዘንድ ሚዛን የሚደፋ ነው።
ከተጠቀሱትም ወራት ውጭ ሌሎችም አስተያየቶች አሉ።
3. ሚዛን የሚደፋውን ወር ስንመርጥ ደግሞ “ረቢዑል አወል ስንተኛው ቀን ላይ?” የሚል ጥያቄ ይከተላል። ይህን ጥያቄ የሚመልስ ዘገባ በ“ኩቱቡ ሲታ” (ቡኻሪ፣ ሙስሊም፣ አቡ ዳውድ፣ ነሳኢይ፣ ቲርሚዚና ኢብኑ ማጃህ) ውስጥ የለም። ከሌሎች የሐዲሥ ጥራዞችም ውስጥ አይገኝም። ይልቁንም የነብዩን ﷺ ገድል በመፃፍ የበለጠ ጥንታዊ የሚባሉት የታሪክ ፀሐፊ ኢብኑ ኢስሓቅ ረቢዑል አወል 12 እንደተወለዱ አስፍረዋል። ያሰፈሩት መረጃ ግን የሰነድ መቆረጥ (ኢንቂጧዕ) አለበት።
ሌላኛው ጥንታዊ የሆኑት የዘርፉ አጥኚ በ 230 ሂ. የሞቱት ኢብኑ ሰዕድ ሲሆኑ እሳቸው ደግሞ ነብዩ ﷺ የተወለዱበት ቀን ላይ የተሰጡ ቀደም ያሉ የተለያዩ ሀሳቦችን ሲጠቅሱ ረቢዑል አወል 2 እና ረቢዑል አወል 10 ያሰፈሩ ሲሆን በስፋት የሚታወቀውንና ዛሬ መውሊድ የሚወጣበትን ረቢዑል አወል 12ን ግን ከነጭራሹ አላወሱትም። በዚህ ላይ የተሰጡ ሃሰቦችን ስናጠቃልል፡-
1. ረቢዑል አወል 1 ነው ያሉ አሉ። [አልኢሻራህ ኢላ ሲረቲልሙስጦፋ፡ 57]
2. ረቢዑል አወል 2 ያሉ አሉ። የአቡ መዕሸር አስሲንዲ (171 ሂ.) እና የኢብኑ ዐብዲል በር (463 ሂ.) ምርጫ ነው። ይሄ ቀን በኢብኑ ሰዕድና በአልዋቂዲ ከተዘረዘሩ ሀሳቦች ውስጥ ነው።
3. ረቢዑል አወል 8 ያሉ አሉ። ከዙህሪ (128 ሂ.) የተዘገበ ሲሆን የኢብኑ ሐዝም (456 ሂ.) እና የኸዋሪዝሚ ምርጫ ነው። የታሪክ ሰዎች ይሄኛውን ትክክለኛ ነው ማለታቸውን ኢብኑ ዐብዲል በር ገልፀዋል። ሌሎችም በዚህ ላይ ተጉዘዋል። የመጀመሪየውን የመውሊድ ኪታብ የፃፉት ኢብኑ ዲሒያም ይሄኛው ሚዛን የሚደፋ አስተያየት እንደሆነ ገልፀዋል።
4. ረቢዑል አወል 10 ያሉም አሉ። ከታቢዒዩ አሽሸዕቢ (100 ሂ.) እና የነብዩ ﷺ ዘር ከሆኑት አቡ ጀዕፈር አልባቂር (114 ሂ.) የተዘገበ ሲሆን የአልዋቂዲ (207 ሂ.) ምርጫ ነው።
5. ረቢዑል አወል 12 ያሉም አሉ። የኢብኑ ኢስሓቅ ምርጫ እንደሆነ አሳልፈናል። ኢብኑ አቢ ሸይባ በዘገቡት ከኢብኑ ዐባስና ከጃቢር ይህን የሚገልፅ ዘገባ አለ። ሆኖም ግን ለመረጃነት ብቁ አይደለም። የሰነድ መቆረጥ እንዳለበት ኢብኑ ከሢር ገልፀዋል። [አልቢዳያ ወንኒሃያ፡ 3/109]
6. ረቢዑል አወል 17 የሚል ከሺዐዎች የተላለፈ ሲሆን ዛሬም ሺዐዎች መውሊድን የሚያከብሩበት ቀን ነው።
7. ረቢዑል አወል 18 ያሉም አሉ። [አልመዋሂቡ አልለዱንያህ፡ 1/131-132]
8. ረቢዑል አወል 22 ያሉም አሉ።
9. ረቢዑል አወል 9 ያሉም አሉ። አንዳንድ ሙስሊም የስነ ፈለክና የሂሳብ ሊቃውንት፣ እንዲሁም እነሱን የተከተሉ ምሁራን “ነብዩ ﷺ እንደተወለዱ የተናገሩበትን ሰኞ ቀን ወደ ኋላ ስንቆጥር የምናገኘው ረቢዑል አወል 12 ላይ ሳይሆን 9 ላይ ነው” ይላሉ። ለምሳሌ የታዋቂው የ“ረሒቁን መኽቱም” ኪታብ አዘጋጅ ሶፍዩርረሕማን አልሙባረክፑሪ፣ ታዋቂው ግብፃዊ የስነ-ፈለክ ምሁር መሕሙድ ባሻ (1885) እና ኡስታዝ ሙሐመድ አልኹደይሪ ተጠቃሽ ናቸው።
ከነዚህ ሃሳቦች ቀደምት ምሁራን ዘንድ ክብደት የነበራቸው ረቢዑል አወል 8 እና ረቢዑል አወል 10 ነበሩ። በተለይም ደግሞ የመጀመሪያው ይበልጥ ክብደት ይሰጠው ነበር። በአሁኑ ሰዓት ይበልጥ የሚታወቀው ግን ረቢዑል አወል 12 ነው። ይህ ሁሉ የተለያየ ሀሳብ ባለበት ለምን 12ኛው ጎልቶ ወጣ? ሁለት መላምት ሲሰጥ አጋጥሞኛል።
1. ይህን ሀሳብ ያንፀባረቁት ኢብኑ ኢስሓቅ ታዋቂነት አንዱ ምክንያት ነው። የኢብኑ ኢስሓቅ “አስሲየር ወልመጋዚ” ወይም “ሲረት ኢብኑ ኢስሓቅ” በዘርፉ ላይ ቀዳሚ ምንጭ ነው። ከሳቸው በኋላ የመጡ በርካታ ፀሐፊዎች የሳቸውን ስራ ነው የገለበጡት። በዚህም ሳቢያ የሳቸው ኪታብ ላይ የሰፈረው ረቢዑል አወል 12 ይበልጥ ሊስፋፋ ችሏል።
2. ሌላኛው ይህኛውን ቀን ይበልጥ ታዋቂ ያደረገው ምክንያት ምናልባትም የመውሊድ አክባሪዎች ይህንን ቀን መምረጣቸው ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ መውሊድን የጀመሩት “ፋጢሚዮች” እራሳቸው በዚህ ቀን ነበር የሚያከብሩት። ዛሬም ላይ ያለው ሁኔታ የምናየው ነው። ስለዚህ የመውሊድ በየሀገሩ መስፋፋት ይሄኛው ቀን ይበልጥ እንዲጎላ አድርጎታል። ምናልባት ለዚህም ሊሆን ይችላል የመውሊድ ፅንሰ-ሀሳብ ከመሰራጨቱ በፊት የነበሩት ኢብኑ ዐብዲል በር “የታሪክ ሰዎች ዘንድ ይበልጥ ታዋቂው ረቢዑል አወል 8 ነው” ሲሉ መውሊድ ከተስፋፋ በኋላ የመጡት ኢብኑ ከሢር ግን ይበልጥ ታዋቂው ረቢዑል አወል 12 ነው ማለታቸው።
ያም አለ ይህ ትክክለኛው ነብዩ ﷺ የተወለዱበት ቀን ስንተኛው እንደሆነ እርግጠኛ በሆነ መልኩ አይታወቅም። በአስተማማኝ ሰነድ የተደገፈ ጠንካራ ማስረጃ ማቅረብም አይቻልም። የክብደታቸው ልዩነት እንዳለ ሆኖ ሊቀርቡ የሚችሉት ያልተጣሩ መረጃዎች ናቸው። ከነዚህ ውስጥ ደግሞ ይበልጥ ክብደት ያለው ረቢዑል አወል 8 ሲሆን፣ ረቢዑል አወል 12 ደግሞ ይበልጥ ታዋቂው ሆኗል። “የለም ረቢዑል አወል ሁለት ነው” ወይም ደግሞ “ረቢዑል አወል 10 ነው”፣… የሚሉትንም “ተሳስታችኋል” ለማለት የሚያስደፍር አሳማኝ ማስረጃ ማቅረብ አይቻልም።
ብቻ የሺዐዎቹን ሃሳብ ጨምሮ ቢያንስ ዘጠኝ የተለያዩ ሀሳቦችን እናገኛለን። እነዚህ ወሩ “ረቢዑል አወል ነው” በሚለው ላይ አንድ አይነት አቋም ያላቸው ናቸው። እንጂ በወሩም ላይ የተለያዩ ሃሳቦችን የሰነዘሩትን ጨምረን ስንቆጥር መላ ምቶቹ ቁጥራቸው ከፍ ይላል። ከዚህም አልፎ በአመቱ ላይ ሳይቀር የተለያዩ ሀሳቦች የሰነዘሩ አሉ። ኢብኑ ሐጀር ረሒመሁላህ እንደሚሉት ኢስላማዊውን አቆጣጠር ለመጀመር ሲታሰብ አራት አማራጮች ነበሩ። እነሱም ነብዩ ﷺ የተወለዱበት ጊዜ፣ መልእክተኛ የተደረጉበት ጊዜ፣ ከመካ ወደ መዲና የተሰደዱበት ጊዜ እና የሞቱበት ጊዜ ናቸው። ስደታቸው (ሂጅራ) የተመረጠበት ምክንያት የተወለዱበትና የተላኩበትን ጊዜ በተመለከተ አመቱን ለይቶ በመወሰን ላይ ንትርክ ስለማይጠፋ ሲሆን ህልፈታቸውን በተመለከተ ደግሞ ሁሌ ሀዘንን ስለሚያስታውስ ምርጫቸው አልሆነም። በዚህም ሳቢያ ሂጅራን በመምረጥ ላይ ሊወስኑ ችለዋል። [ፈትሑል ባሪ፡ 7/268] የነዚህ የተለያዩ ዘገባዎች መምጣት መውሊድ በሸሪዐችን ውስጥ ቦታ እንደሌለው የራሱ ትልቅ መልእክት አለው። ይህም ምን ማለት ነው?
1. ሶሐቦች፣ ታቢዒዮች፣ አትባዑ ታቢዒንና ቀደምት የሙስሊም ምሁራን በዚህ ቀን ላይ የተለያየ ሀሳብ መሰንዘራቸው በዚህ ረገድ ግልፅ መረጃ አለመኖሩን ያሳያል። ይህም የመውሊድ አመታዊ በዓል እነሱ ዘንድ እንዳልነበር ግልፅ መልእክት አለው። በርግጥ ለመውሊድ ይሁንታ የቸሩት ሳይቀሩ ይህን ሐቅ በመናገር ገላግለውናል።
2. የተለያዩ ሀሳቦች መተላለፋቸው የሰለፍ ምሁራን ዘንድ ጉዳዩ ኋላ ላይ የተሰጠውን ያክል ክብደት እንዳልተሰጠው ያሳያል።
3. መውሊድ በኢስላም ውስጥ ቦታ ቢኖረው ኖሮ ነብዩ ﷺ የተወለዱበትን ቀን አላህ በቁርኣን ወይም በሐዲሥ ግልፅ እንዲሆን ያደርገው ነበር። ጌታዬ {አይሳሳትም አይረሳምም።} [ጦሀ፡ 52] ስለዚህ ግልፅ አለመደረጉ በሸሪዐው ቦታ እንደሌለውና ከዲንም እንዳልሆነ ያሳያል።
በሌላ በኩል እነዚህ እንቁ የሆኑ የወርቃማው ዘመን ትውልዶች (ሶሐቦች፣ ታቢዒዮችና ተከታዮቻቸው) ዛሬ ለመውሊድ የሚሟገቱ ሰዎች የሚያቀርቧቸውን የቁርኣን አንቀፆችና ሐዲሦች ከማንም በላይ እንደሚያውቋቸው ግልፅ ነው። ይሁን እንጂ “አሃ እነዚህ እኮ መውሊድ መከበር እንዳለበት ይጠቁማሉ። ስለዚህ ለምን ነብዩን ﷺ በስንተኛው ቀን እንደተወለዱ አንጠይቃቸውም?” አለማለታቸው ጉዳዩ ትኩረት የሚገባው እንዳልሆነ ይጠቁማል። ነገር ግን “ካፈርኩ አይመልሰኝ” ያሉ ሱፍዮች አይናቸውን በጨው አጥበው “ሶሐቦች መውሊድን አክብረዋል” ሲሉ ይሰማሉ። የሐያእ መቅለል ከዚህም በላይ በላይ ያናግራል። “ካላፈርክ ያሻህን ስራ” አይደል የተባለው?
ምናልባት “የተወለዱበት ቀን በቁርጥ አለመታወቁ አያስጨንቀንም፡፡ በተመቸን ቀን እናከብረዋለን” የሚሉ ከሆነ የልደት ቀናቸው በውል የማይታወቁ በቁርኣን የተዘረዘሩ ነብያን መውሊድም ሊያከብሩ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ግና ትኩረታቸው ከአባት ከአያት የተወሰደን ውርስ ማስቀጠል እንጂ በንፁሕ አእምሮ ሐቅን መፈለግ አይደለም፡፡
ከ “መውሊድ፤ ታሪክ፣ ግድፈት፣ እርምት” መፅሐፍ ተነካክቶ የተወሰደ


Ibnu Munewor 

Post a Comment

0 Comments