Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

የ«ኺላፍ» ጉዳዮች!

بِسْمِ اللَّهِ الرَّحْمَنِ الرَّحِيمِ...ባጭሩ... ስለ ኢስላማዊ ህግጋት ሊኖረን የሚገባውን ምልከታ በሁለት ከፍለን ልናይ እንችላለን፦1ኛ.= በርዕሶቹ ላይ የሚሰጠው  ሸሪዓዊ ፍርድ በግልጽ ቁርአናዊና ነቢያዊ አስተምህሮቶች የተቋጨና በቀደምት ዑለማዎች ሙሉ ስምምነት የፀደቀ እንደሆነ ለየትኛውም ዓይነት ውዝግብ መድረክ አይኖርም፤ ብይኑንም ያለምንም ማንገራገር ተቀብሎ ማስተናገድ የግድ ይሆናል። ይህንን እውነታ ከተረዳ በኋላ በጉዳዩ ላይ ከተመለከተው ሸሪዓዊ ህግ ጋር የሚጣረስ አቋም ያንፀባረቀ ካለ አስፈላጊ ሲሆን እንደ ጥፋቱ መጠንና ተፅዕኖ ስህተተኝነቱን በግልጽ አንደበት ማስፈር ይገባል፤ ጥፋቱም ተቀባይነት የሚያስገኝ ምክንያት ስለማይኖረው አቋሙ እንደማፈንገጥ ታስቦ የእርምት እርምጃ ይወሰድበታል፤ አልፎ ተርፎም የሚከተለው የአላህ ቃል የሚመለከተው ሊሆን ይችላል፦
وَمَنْ يُشَاقِقِ الرَّسُولَ مِنْ بَعْدِ مَا تَبَيَّنَ لَهُ الْهُدَى وَيَتَّبِعْ غَيْرَ سَبِيلِ الْمُؤْمِنِينَ نُوَلِّهِ مَا تَوَلَّى وَنُصْلِهِ جَهَنَّمَ وَسَاءَتْ مَصِيرًا النساء: 115
«(የ)ምራቻ (መንገድ) ከተገለጠለት በኋላ መልዕክተኛውን የሚፃረርና ከሙእሚኖች መንገድ ሌላ የሚከተል የመረጠውን (ጥመት) እናሸክመዋለን! (ወደ ዞረበት እናዞረዋለን)፤ ጀሀነምም እናስገባዋለን፤ ከመመለሻነቷ (አንፃር)ም የከፋች ሆነች!»ታዋቂው የኢስላም ጠቢብና ሊቅ ኢብኑ ተይሚያህ እንዲህ ይላሉ፦
مَنْ خَالَفَ الْكِتَابَ الْمُسْتَبِينَ وَالسُّنَّةَ الْمُسْتَفِيضَةَ أَوْ مَا أَجْمَعَ عَلَيْهِ سَلَفُ الْأُمَّةِ خِلَافًا لَا يُعْذَرُ فِيهِ فَهَذَا يُعَامَلُ بِمَا يُعَامَلُ بِهِ أَهْلُ الْبِدَعِ..
«ግልፅ ያለውን (የ)ቁርኣን (አስተምህሮት)፣ የተሰራጨውን ነብያዊ ፈለግ አሊያም የዚህ ህዝበ-ሙስሊም ቀደምት ትውልዶች (በአንድ አቋም) የተስማሙበትን ጉዳይ ይቅርታ ሊደረግለት በማይገባ መልኩ (ዑዝር በማያሰጥ መልኩ) የጣሰ  የቢድዓ አንጃዎች በሚስተናገዱበት (ስርዓት) ይስተናገዳል (= የነርሱ ብይን ይሰጠዋል)።» {መጅሙዑ’ል-ፈታዋ [24/172]}.

ለዚህ ክፍል ምሳሌ ሊሆኑ የሚችሉ በርካታ ድንጋጌዎች አሉ፤ ከአላህ በቀር ማንንም (የአምልኮ ጥሪ) አለመጣራት፣ የአላህ ስሞችንና ባህሪያቱን መልዕክታቸውን ሳያዛቡ በተገቢው መልኩ ተቀብሎ ማስተናገድ፣ ኢማን መልካም ንግግርንና ተግባርን እንደሚያካትት ማርጋገጥ፣ በቀደር በአግባቡ ማመን፣ ከቢድዓ መጠንቀቅ…ወዘተ እነኚህ ከኢስላም ህልውና ጋራ ቀጥተኛ ዝምድና ያላቸው ጉዳዮች ላይ ምንም አይነት ቦታ የሚሰጠው “ኺላፍ” (ውዝግብ) የለም!
- አንዳንድ ግለሰቦች  (ለምሳሌ፦ ስለ አላህ ባህሪያት አንድ ሙስሊም ሊኖረው የሚገባው ትክክለኛ አቋም ሲገለፅ) በርዕሱ ላይ የኢስላም ሊቃውንት ተወዛግበዋል!” የሚሉት አባባል ፍፁም የተሳሳተና አደገኛ ድምዳሜ ነው። ብዙዎች ይህን መሰል ቃል የሚሰነዝሩት እውነታውን በተገቢው መልኩ ለመረዳት ከሚደረግ ውይይት ለመሸሽ ሲሆን ሌሎች ደግሞ ከግንዛቤ እጥረት በመጣ የዋህነት ነው። ሆኖም ከሶስቱ ምርጥ ትውልዶች በኋላ ከመጡት የኋለኞቹ ሊቃውንት መካከል አንዳንዶቹ እንደሌሎች ርዕሶች ሁሉ በዚህኛውም ላይ በተለያዩ ምክንያቶችና ትፅዕኖዎች የተነሳ ስህተት ላይ መውደቃቸው ይታወቃል። ይህ አቋማቸው ግን እንደ ስህተት ታይቶ ይታረማል እንጂ የቀድሞዎቹን ትውልዶች ስምምነት የሚንድ "ኺላፍ" በፍፁም አይሆንም! አዎን! ለተሳሳቱ ዓሊሞች የሚሰጠው ማስተካከያ በቢድዓ አራማጅ ጎጠኞች ላይ እንደሚደርሰው ውግዘት አይደለም! ግን ስህተት ሁሉ እንደ መደበኛ <ኺላፍ> ሚዛን ላይ አይሰቀልም፤ በርዕሱ ላይ የሚሰጠው ሸሪዓዊ ፍርድ በግልጽ ቁርአናዊና ነቢያዊ አስተምህሮቶች የተቋጨና በቀደምት ዑለማዎች ሙሉ ስምምነት የፀደቀ ስለሆነ ውዝግብን የሚያስተናግድ መድረክ አይኖረውምና!
2ኛ.= በርዕሶቹ ላይ የሚጠቀሱት ማስረጃዎች የሚጠቁሙትን መልዕክት በተመለከተ ቀደምት የኢስላም ሊቃውንት በግንዛቤ ልዩነት የተለያየ አቋም ያንጸባረቁ ከሆነናና ጉዳዮቹ በዑለማዎች ዘንድ ሸሪዓዊ ምልከታን (ኢጅቲሃድን) የሚያስተናግዱ መሆናቸው የታወቀ እንደሆነ አንድ ዓሊም በዚህ ረገድ ከሌላው የተለየ አቋም ቢመርጥ፣ ብሎም ቢሳሳት ፍርዱ እንደሙሉ ጥፋት ተወስዶ አይኮነንም፤ መልዕክተኛው እንደዚህ ብለዋል፦

  إِذَا حَكَمَ الْحَاكِمُ فَاجْتَهَدَ ثُمَّ أَصَابَ فَلَهُ أَجْرَانِ وَإِذَا حَكَمَ فَاجْتَهَدَ ثُمَّ أَخْطَأَ فَلَهُ أَجْرٌ«አንድ ፈራጅ ሲፈርድ (እውነታን ለመረዳት) ተጣጥሮ ትክክል ከሆነ ሁለት ምንዳ(አጅር) አለው፤ ሲፈርድ (እውነታን ለመረዳት) ተጣጥሮ ከተሳሳተ አንድ አጅር አለው!» (አል-ቡኻሪ/ 7352 ፣ ሙስሊም / 1716)
ሆኖም የላይኛው "ሀዲሥ" እንደሚያስረዳው በዚህኛውም ርዕስ ላይ ቢሆን እውነትን ለማወቅ ሁሉም እንደየአቅሙ መጣር ይጠበቅበታል።
አላህ ሁላችንንም ወደ ጀነት ጎዳና ይምራን!