Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ሁላችንም ኃላፊነታችንን እንወጣ

ሁላችንም ኃላፊነታችንን እንወጣ
~~~~~~~~
– ወደ ቤተሰብ የተመለሳችሁ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የካባቢያችሁን ማህበረሰብ የማንቃት ስራ ስሩ። አብዛኛው ህዝባችን ሰበብ ለማድረስ እንኳን አሻፈረኝ እንዳለ ነው። በርግጥ ኑሮው ከእጅ ወደ አፍ ለሆነው ህዝባችን ብዙ የጥንቃቄ እርምጃዎችን ለመውሰድ ይቸገራል። ነገር ግን አቅም የማይጠይቁ ነገሮችንም ለመተግበር ተነሳሽነት አይታይበትም። ስለዚህ ቢቻል ከፈቃደኞች ጋር በመተባበር፣ ካልሆነ የራሳችሁን ድርሻ ተወጡ። 
– በየወረዳውና በየቀበሌው ያላችሁ ኃላፊዎች እባካችሁ ህዝባችሁን ለመጠበቅ የድርሻችሁን ተወጡ። በማይክራፎን እየዞራችሁ ትምህርት ስጡ። መጠጥ ቤቶችን፣ ሺሻ ቤቶችን፣ ጫት ቤቶችን ዝጉ። ለገበያ ቀናት መላ ፈልጉ። ለሰርግና ለለቅሶ ሰው እንዳይሰባሰብ እቀባ ጣሉ። የህዝብ መጓጓዣዎችን በተመለከተ የሌሎች አካባቢዎችን ተሞክሮ ውሰዱ። የማስታወቂያ ብሮሸሮችን በትኑ።
– ወገኔ ሆይ! "አላህ አለን" እያልክ አታንቀላፋ። አላህ ሰበብ አታድርስ አላለህም። ለመካሪ የማትመች አጉል ፍጡር አትሁን። ሰዎች ለራስህ ደህንነት ተቆርቁረው ሲመክሩህ ጀሮ ዳባ ልበስ አትበል። ይሄ ማንቀላፋት እንጂ ተወኩል አይደለም። ስለዚህ ከአላስፈላጊ ቅልቅል ራቅ። ተራራቅ። እጅህን ታጠብ። ከመጨባበጥ ተቆጠብ። አንተ ግን ጭራሽ እየተሳሳምክ ነው። ለኛ አይነት ባንድ ክፍል ውስጥ ታጭቆ ለሚኖር ማህበረሰብ የአንድ ሰው መበከል የመላው ቤተሰብ መበከል ስለሆነ አትዘናጋ። ቀለል ያሉ ጉዞዎችን ከማንም ጋር ሳትጋፋ በእግርህ ተጓዝ። እራስህን ከተጠራጠርክ እራስህን ከቤተሰብ አግልለህ ለሚመለከተው ክፍል ባስቸኳይ አሳውቅ። አይበለውና በዚህ ቫይረስ ከተጠቃህም ተረጋጋ። የሚያስፈልጉትን እርምጃዎች በተክክል ተግብር። ቤተሰብህንና ወገንህን እንዳትበክል ጥንቃቄ አድርግ። እራስህን ሳትደብቅ ባስቸኳይ ሃኪም አማክር። በመደበቅ የምትከስረው እንጂ የምታተርፈው የለም። ትራንስፖርት ላይ ታጭቀህ አትጓዝ። ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እየተነጋገርክ ለመቅረፍ ሞክር። ካልሆነ በእግርህ ተጓዝ። በተቻለ መጠን በቤትህ ርጋ። እንቅስቃሴ ቀንስ።
– እስከ ታች ጤና ኬላ ድረስ ያላችሁ የጤና ባለሙያዎች በቅድሚያ ለራሳችሁ ተገቢውን ጥንቃቄ አድርጉ። የናንተ ጤንነት ለማህበረሰባችሁ ምን ያክል ዋጋ እንዳለው የምታውቁት ነው። የናንተ መታመም የህብረተሰብ መበከል ነው። የናንተ የጥንቃቄ እርምጃ ለህዝቡ በተለይም ለታካሚው የሚያስተላልፈው መልክት አለው። ከዚህም ባለፈ እያስተባበራችሁ ሰፊ ንቅናቄ አድርጉ።
– ዱዓቶችና መሻይኾች ወገናችሁን ከዚህ ፈተና ለማትረፍ የምትችሉትን ሰበብ እያደረሳችሁ ነው ወይ? እራሳችሁን ጠይቁ። ሰዎችን ወደ አላህ እንዲመለሱ፣ በተለይም ከሺርክና ከባባድ ወንጀሎች እንዲቶብቱ ወትውቱ። ሰው ሲጨንቀው ወደ ሺርክና ቢድዐ ስለሚያዘነብል ሰፊ የማንቃት ስራ ስሩ። ሰዎች ሰበብ ለማድረስ እየተዘናጉ ስለሆነ በዚህም በኩል ትልቅ ስራ መስራት ይጠይቃል። ሰው ከሌላ ይልቅ የሃይማኖት አስተማሪዎችን ይሰማልና ተገቢ ትኩረት ስጡ።
– የመጓጓዣ ባለቤቶች ሆይ! የእለት ትርፍ እያያችሁ እራሳችሁንም ወገናችሁንም አደጋ ላይ አትጣሉ። ሳንቲም ከጤናና ከህይወት በላይ አይደለም። በወገን ኪሳራ አተርፋለሁ ማለት ሞኝነት ነው። "አልጠግብ ባይ ተፍቶ ያርፋል።"
– ነጋዴዎች ሆይ! አላህን ፍሩ። ርህራሄ ይኑራችሁ። "በምድር ላለ እዘኑ። በሰማይ ያለው ያዝንላችኋል" ብለዋል ነብያችን ሶለ፞ላ፞ሁ ዐለይሂ ወሰለ፞ም። መጨካከኑ ተያይዞ መጥፋት ነው። መደበቅ ሳይሆን ለህዝብ የሚያስፈልጉ ፍጆታዎችን በተመጣጣኝ ዋጋ አቅርቡ። ለሁሉም የሚበጀው መከራን ተደጋግፎ ማለፍ ነው።

(ሼር አድርጉት፣ ባረከላ፞ሁ ፊኩም)

Post a Comment

0 Comments