Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

የዱንያ ነገር!!


***የዱንያ ነገር!!***
~~~~~~~~~~~~~~~
ዐልይ ኢብኑል ሀይሠም እንዲህ ይላሉ:–
"አምሳያ ያላየሁለት የዘመን መገለባበጥ፣ የጊዜ መለዋወጥ አይቻለሁ።
★ የአልፈድል ኢብኑ ረቢዕ ንብረት በአንድ ሺህ ግመል ተጭኖ አይቻለሁ። ሌላ ጊዜ ግን ጠቅላላ ንብረቱ አንዲት ዘንቢል ውስጥ ሆና ተደብቄ አይቻለሁ። በውስጧ መድሃኒቶቹ ተጨምረው።
★ አልሐሰን ኢብኑ ሰህልን ደግሞ ጠቅላላ ንብረቱ አንዲት ዘንቢል ውስጥ ሆና ተመልክቻለሁ። ከዚያ ግን ንብረቱ በአንድ ሺ ግመል ላይ ተጭኖ አይቸዋለሁ።"
||
ዱንያ እንዲህ ነች። መርጋት የማታውቅ ወላዋይ!!
 ሃያላን ይዋረዳሉ። ደካሞች ይነግሳሉ።
 ሀብታሞች ጎዳና ላይ ይወድቃሉ። ምንዱባን በሰማይ ጠቀስ ህንፃ ይንፈላሰሳሉ።
 ሳር ቅጠሉን የተፀየፈው ጨፍጫፊ አረመኔ አለም ጠባው ከአይጥ ጎሬ ሲያደፍጥ ታየዋለህ። የትላንቱ ተሳዳጅ ተራውን ሲያሳድድ ትመለከታለህ።
® ይሄው ነች ዱንያ!! ብልጭ ብላ ድርግም፣ ቦግ ብላ እልም የምትል። ሁሌ ሳቅ የለም! ሁሌ ድል የለም።
|
 በድር ላይ ለያዥ ለገናዥ ያስቸገሩ፣ ጥጋብ ያስከራቸው ቁረይሾች፣ 70 መኳንንቶቻቸው ትላንት ሲያሳድዷቸው በነበሩ ሶሐቦች ሰይፍ ተበልተው፣ ሌላ 70 ደግሞ በምርኮ አስረክበው የሐዘን ማቅ ለብሰዋል። መካ በዋይታ ተንጣለች።
|
 ኡሑድ ሌላ ቀን ነው። ሌላ ተራ!! አጋሪዎች የፈነደቁበት፣ እነ ሐምዛን፣ እነ ሙስዐብን ጨምሮ ከ70 በላይ ታላላቅ ጀግኖች ወድቀው ሌላ 70 የቆሰሉበት፣ አሳዝኝ ክስተት እውን የሆነበት ቀን። ሶሐቦች አካላቸው በስለት፣ ልባቸው በሐዘን ቢቆስል ጊዜ አላህ እንዲህ ሲል አሳሰባቸው: –
(إِنْ يَمْسَسْكُمْ قَرْحٌ فَقَدْ مَسَّ الْقَوْمَ قَرْحٌ مِثْلُهُ ۚ وَتِلْكَ الْأَيَّامُ نُدَاوِلُهَا بَيْنَ النَّاسَ)
"ቁስል ቢያገኛችሁ ሰዎቹንም መሰሉ ቁስል አግኝቷቸዋል፡፡ እናም እነዚህን ቀናት በሰዎች መካከል (በመልካምና በሌላ) እናቀያይራቸዋለን፡፡" [ኣሉ ዒምራን: 140]
|||
ዱንያ አመሏ ነው። ዛሬም እንዲሁ ናት።
ግን ማነው የሚማረው? ግን ማነው የሚመረምረው? ግን ማነው የዱንያን ከንቱነት ተገንዝቦ ለዘላለም ቤቱ ከልብ የሚጨነቀው?
እስከ መቼ ነው የምናንቀላፋው?
እስከ መቼ ነው የምንዘናጋው?
እስከ መቼ ነው በከንቱ የምንባዝነው?
ኢንና ሊላሂ ወኢንና ኢለይሂ ራጂዑን!!
ኢላሂ ልብ ስጠን!!

Post a Comment

0 Comments