Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ዋቄፈና/Waaqeffannaa .


#ዋቄፈና/Waaqeffannaa
.
.
ዋቄፈና በሀገራችን ከሚገኙ ዘልማዳዊ እምነቶች አንዱ ነው። በማእከላዊና ደቡባዊ ኢትዮጵያ ጥቂት የማይባሉ ተከታዮች የቀሩት እምነት ነው።
.
ከቅርብ አመታት ወዲህ ግን የብሄር ፓለቲካውን መነሳሳትን ተከትሎ ይህን ከጊዜ ጊዜ እየተመናመነ የሄደ ዘልማዳዊ እምነት መልሶ ለማንሳት የሚታትሩ ሰዎችን እያየን ነው።
.
.
#ዋቄፈና ምንድን ነው?
.
.
ስለዋቄፈና እምነት የሚገልፅ የእምነቱ መመሪያ መፅሀፍ የለም። እንዳውም ያለፈ ታሪኩን እንኳ የሚገልፅ ጥንታዊ ሰነድ አይገኝም። እንደ ተከታዮቹ ግንዛቤ በአንደበት ከሚተላለፈው እሳቤ በዘለለ የተጨበጠ እና አንድ አይነት ምልከታን የሚያስይዝ የጋራ ስምምነት የለውም። ለዛም ነው ዋቄፈና 'ዘልማዳዊ እምነት' የምንለው።
.
ዋቄፈና - ዋቃ/Waaqaa ከሚለው ቃል ተወስዶ ለእምነቱ መጠሪያነት እያገለገለ የሚገኝ ስያሜ ነው። ዋቃ በኦሮሚያ አካባቢ በሚገኙ አማኞቹ ዘንድ እንደ አምላክ የሚታሰብ አንዳንዶች ታላቅ ግኝ/Supreme being/ እንደሆነ ሌሎች ደግሞ ፈጣሪ እንደሆነ የሚያምኑበት ነው። 8
.
እምነቱ በከፊል ሰርጎ በገባባቸው እንደ አማራ ክልል ባሉ ቦታዎች 'ውቃቢ' እየተባለ ሲጠራ የሚሰጠው ባህሪ ግን ዋቄፈናዎች ዘንድ ካለው ፍፁም የተለየ ነው።
.
ወንድ የእምነቱ ተከታይ ዋቄፈታ/Waaqeffataa/ ሲባል ዋቄፈቱ/Waaqeffattuu/ ደግሞ ለሴት የእምነቱ ተከታይ የሚሰጥ መጠሪያ ነው፡፡
.
.
#የዋቄፈና እምነቶች
.
.
(እምነቱ የተፃፈ የወል መመሪያ ስለሌለው ከቦታ ቦታ ሊለያይ ይችላል)
.
.
* ዋቄፈናዎች 'ዋቃ' ድሮ ከሰዎች ጋር ይኖር ነበር ይላሉ፤ ሰዎች መጥፎ መስራት ሲጀምሩ ከነሱ ተለይቷል ብለው ያምናሉ።
.
* ዋቃ (አምላክ በነሱ እሳቤ) ጥቁር ነው ብለው ያምናሉ፤ በፀሎታቸውም ጥቁር አምላክ/Waaqaa gurracha ሲሉ ይጠሩታል።
.
* ዋቃን በሰማይ ይመስላሉ፤ መሬትም የዋቃ ሚስት ነች ብለው ያስባሉ። ይህንንም በምርቃትና እርግማኖቻቸው ይገልፁታል።
.
* ዋቃን ለመለማመን ወደ ተራሮች ይወጣሉ፤ እሱም በጥቁር ደመና ተመስሎ ይቀርበናል ብለው ያስባሉ።
.
* ለኦዳ/ዛፍ የተለየ ቦታ ይሰጣሉ። የተለያዩ እምነቶችንም በሱ ላይ ያሳድራሉ፤ ለመሬት መስዋእት ለማቅረብ በኦዳ/ዛፍ ስር ያርዳሉ። (አንዳንዶች የኦዳ ዛፍን እንደ እምነቱ ምልክት በመቁጠር ቅርፁን አንገታቸው ላይ ያስሩታል)
.
* ለምስጋና በሚል በዛፎች፣ በሀይቆችና ተራሮች ላይ የኢሬቻን በዓልን ያከብራሉ። ለዋቃ እርጥብ ሳርን በቁርባን መልክ ውሀ ላይ ይበትናሉ።
.
* 'ቃሉ' በመባል የሚጠሩ የዋቃን መልእክት ለህዝቡ የሚያደርሱ፣ የህዝቡንም ፀሎት ለዋቃ የሚያስተላልፉ ሰዎች አሉ ብለው ያምናሉ። (ቃሉዎች ልክ እንደ ጠንቋዮች ከጅኖች ጋር ቁርኝት እንዳላቸው ይገመታል)
.
[ እምነቱ በከፊል በሰረገባቸው ሌሎች ቦታዎች ጠንቋዮች 'ቃሉ/ቃልቻ' በመባል ይጠራሉ - ሆኖም 'ቃልቻ' የሚለውን ቃል ለሸሆች እንደተለዋጭ ስም የሚጠቀሙም እንዳሉ ልብ ይሏል]
.
* 'አያና' የሚባል የሞቱ ሰዎች መንፈስ አለ ብለው ያምናሉ። ያ መንፈስ በሰዎች ላይ እንደሚያድርም ያስባሉ። መንፈሱ አድሮባቸዋል የሚሏቸውንም ሰዎች አያና/አያንቱ ወይም ቃሉ/ቃሊቲ ብለው ይጠራሉ።
.
* አድባር እና አቴቴ የሚባሉ አማልክት በተለያየ በዓል እና ድግስ መልክ ምስጋናና ልመና ይቀርብላቸዋል።
[ይህ እምነቱ በከፊል በሰረገባቸው ማህበረሰቦችም ዘንድ ይታያል]
.
* የዋቄፈና እምነት ከአስተዳደራዊ የአባገዳ ስርአት ጋር ታሪካዊም መንፈሳዊም ቁርኝት አለው። (ይህንን መካድ የአፄዎቹ ስርዓት ከኦርቶዶክስ ክርስትና ጋር ቁርኝት አልነበረውም ብሎ እንደመሞገት ነው)
.
* ዋቄፈናዎች ከቀብር በኋላ ስላለው ህይወት ጥርት ያለ ምልከታ የላቸውም። በዚህና በሌሎችም አንዳንድ ነጥቦች ላይ ከሌሎች ሰማያዊ ሀይማኖቶች የተኮረጁ እምነቶችን ይቀላቅላሉ።
.
.
ይህ ከላይ የሰፈረው እንግዲህ ስለዋቄፈና እምነት በወፍ-በረር ጥቆማ ይሰጣል። እምነቱ ዘልማዳዊ እንደመሆኑ ያልደረጀ እና በተከታዮቹም ዘንድ ወጥ የሆነ ምልከታ የሌለው ነው።
.
ዋቄፈና ያልተብራሩ እምነቶችን ከመያዙም ጋር ከሌሎች ሃይማኖቶች በተኮረጁ ገለፃዎችም የተጠጋገነ ነው።
.
አንድ የሚያስማማን ነገር ግን እምነቱ በመሰረቱ ከአይሁድ፣ ከክርስትናም ሆነ እስልምና የተለየ መንገድን የሚከተል ግና ከዚህም ከዚያም እየኮረጀ በሁለት እግሩ ለመቆም የሚውተረተር መሆኑ ነው።
.
.
#ዋቄፈና ሌሎች ዘንድ...
.
.
ዋቄፈናን ሰዎች እንዴት እንደሚመለከቱት ስናስተውል ሶስት አይነት ሰዎችን እናገኛለን።
.
1. የመጀመሪያዎቹ ስለ እምነቱ የማያውቁ ሰዎች ሲሆኑ እይታቸው ከቃላቱ በመነሳት በተለይም 'ዋቃ' የሚለውን በመመልከት ብቻ ይህ ቃል የአምላክ የአፋን ኦሮሞ ስም እንደሆነ የሚገምቱና ከዚህ ያለፈ ግንዛቤ የሌላቸው ናቸው።
.
2. ሁለተኛዎቹ ስለእምነቱ ጥቂትም ቢሆን ግንዛቤ ያላቸው እና እምነቱን እንደባዕድ አምልኮ የሚቆጥሩ ናቸው።
.
3. ሶስተኛዎቹ ግን ስለእምነቱ ጥልቅ ግንዛቤ ያላቸው (ምናልባትም የሚያምኑበት) ሆኖም እምነቱን ከኦሮሞ ብሄርተኝነት ጋር በማቆራኘት ለማስፋፋት የሚጥሩና ይህም እንዳይታወቅባቸው በማድበስበስ የተጠመዱ ናቸው።
[እዚህ ጋር ግን ጥልቅ እውቀት ሳይኖራቸው በወገንተኝነት ብቻ ዋቄፈናን ከፍ ከፍ ለማድረግ የሚደክሙም እንዳሉ ልብ ይሏል]
.
የሶስተኛዎቹ ሰዎች ምልከታ ምናልባትም እምነቱን ከመክሰም በመታደግና ዘመናዊ ቁመና በማልበስ ወደ ገበያ ለመመለስ የሚፍጨረጨሩ እንዳሉ ያሳያል።
.
እነዚህ ሰዎች እምነቱ በሌሎች ሀይማኖቶች ዘንድ ጥርጣሬ እንዳያስነሳ ዋቄፈናን ከየሀይማኖቱ ለማመሳሰል ወይም የቃላት ትርጉም እንጂ ልዩነት እንደሌለ ለማሳመን ሲጥሩ ይስተዋላል።
.
በሌላ በኩል ደግሞ ዋቄፈና የኦሪት መሰረት ያለውና እስልምናንም ሆነ ክርስትናን የቀደመ እምነት እንደሆነ ሲደሰኩሩ ይሰማል። አያይዘውም የራሱ መርሆ እና ቀኖና እንዳለው ይሰብካሉ።
.
በግላጭ የሚታዩ የባዕድ አምልኮ ተግባራትን በመካድም ምንም አይነት ባዕድ አምልኮ እንደሌለ እንዳውም እምነቱ አሀዳዊ እንደሆነ ለመግለፅ ይሞክራሉ።
.
.
እኛስ ...
.
.
ከላይ በሶስተኝነት የተጠቀሱት አካላት ሰሞነኛ የፓለቲካ ትኩሳትን ተጠቅመው የተዘነጋውን ዘልማዳዊ እምነት ወደ ፊት ለማምጣት እየተሯሯጡ ነው። ይህን እያዩ ማለፍ ነገ ዋጋ ሊያስከፍል ስለሚችል እንደሙስሊም የምንችለውን ማድረግ ይኖርብናል።
.
እንደሚታወቀው እኛ ሙስሊሞች ሙሉ የሆነ እና ለየትኛውም ዘመን እና ህዝብ የሚመጥን ሀይማኖት ከጌታችን ተሰጥቶናል። ይህም በቁርአንና በነብያችን (ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም) ሱና በበቂ ሁኔታ ተብራርቷል። በዓሊሞቻችን ትግልም ሳይበረዝ እኛ ዘንድ ደርሷል።
.
الْيَوْمَ أَكْمَلْتُ لَكمْ دِينَكُمْ وَأَتْمَمْتُ عَلَيْكُمْ نِعْمَتِي وَرَضِيتُ لَكُمُ الْإِسْلَامَ دِينًا
.
"ዛሬ ሐይማኖታችሁን ሞላሁላችሁ ፀጋዬንም በናንተ ላይ ፈፀምኩ፤ ከሐይማኖትም እስልምናን መረጥኩላችሁ" አል-ማኢዳ 3
.
ከዚህ ሀይማኖት ውጪ የሚሻ ወይም የሌላን አመለካከት ማስረግ የሚፈልግ ከቀጥተኛው ጎዳና እንደሚወጣና ራሱንም ለጥፋት እንደሚያጋልጥ በማስጠንቀቂያ ተናግሯል።
.
.
وَمَن يُشَاقِقِ الرَّسُولَ مِن بَعْدِ مَا تَبَيَّنَ لَهُ الْهُدَىٰ وَيَتَّبِعْ غَيْرَ سَبِيلِ الْمُؤْمِنِينَ نُوَلِّهِ مَا تَوَلَّىٰ وَنُصْلِهِ جَهَنَّمَ ۖ وَسَاءَتْ مَصِيرًا
.
"ቀናው መንገድ ከተገለጠለት በኋላ መልእክተኛውን የሚፃረር እና ከምእመናን መንገድ ሌላን የሚከተል በተሾመበት (ጥመት ላይ) እንሾመዋለን፣ ጀሀነምም እንዶለዋለን፣ መመለሻይቱም ከፋች" አ'ኒሳዕ 115
.
ስለሆነም የህይወት መመሪያችን የሆነውን እስልምና አጥብቀን በትክክለኛው ጎዳና እንዘልቅ ዘንድ ከእንዲህ አይነት የባህል ካባ የደረቡ እምነቶች ሙሉ በሙሉ ከመዘፈቅም ሆነ ጥቂቱን ከመቀበል ራሳችንን ልንጠብቅ ይገባል።.
.
ከዚህም ባሻገር አላዋቂ ወንድሞቻችን ተሳስተው ወደ ጥፋት እንዳይገቡ ልንታደጋቸው ይገባል። እንዲሁም እምነቱ እንደ ክርስትናና አይሁድ እምነት እንደማይቆጠር የነርሱንም ሑክም/ብያኔ እንደማያገኝ ልብ ማለት ያስፈልጋል።
.
ነገር ግን ስለዋቄፈና ስንናገር ጉዳዩን ከብሄር ጋር በማቆራኘት ከመቃወምም ሆነ ከመከላከል ልንቆጠብ ይገባል። ሁለቱም አካሄድ የማንፈልገውን ያመጣልና።
.
በመጨረሻም ጉዳዩ የተለየ ትኩረት ተሰጥቶት ዓሊሞችና ዱዓቶች ህዝቡ በሚረዳው ቋንቋ ትምህርት እንዲሰጡ ማስታወስ ያስፈልጋል።
.
.
አላህ በቀናው መንገድ ላይ ያፅናን!

Post a Comment

2 Comments

  1. it is good keep it up

    ReplyDelete
  2. የተውሂዱም የክርስትናውም ቀደምት ነው

    ReplyDelete