Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ከሃሜት ለመራቅ የሚያግዙ 11 ነጥቦች




ከሃሜት ለመራቅ የሚያግዙ 11 ነጥቦች
አላህ ያደለው በጣም ጥቂት ሰው ካልሆነ በስተቀር ከሃሜት ወንጀል የሚተርፍ የለም፡፡ እንዲያውም “እነ እከሌ ሃሜተኞች ናቸው” እያሉ ሌሎችን የሚወነጅሉ ሰዎች እራሱ በአብዛሀኛው እራሳቸውም ሃሜተኞች ናቸው፡፡ ልዩነቱ ለሃሜት የሚገፋው ምክንያትና የሚታማው አካል መለያየት ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ ችግር አብዛሀኞቻችን የተዘፈቅንበት ነው፡፡ ከዚህ በፊት ሰለሃሜት በፃፍኩት ስር “እንዴት ከሃሜት መራቅ እንችላለን?” የሚል ጥያቄ ከተወሰኑ ወንድም እህቶች ተሰንዝሮ ነበር፡፡ ብዘገይም በዚህ ረገድ አጋዥ የመሰሉኝን ጥቂት ነጥቦች እንደሚከተለው አስፍሬያለሁ፡፡ (ኔትወርክ ደካማ ስለሆነ የባለፈውን ፅሁፍ ሊንክ እዚህ ላይ ማያያዝ አልቻልኩም፡፡)
① የሃሜትን ምንነት መረዳት፡- ብዙ ሰዎች ሰዎችን እያሙ ነገር ግን “ይሄ እውነት ነው፤ ሃሜት አይደለም” ሲሉ ይደመጣሉ፡፡ ይሄ ስለሃሜት ያላቸውን የግንዛቤ ክፍተት የሚያሳይ ነው፡፡ ሃሜት ማለት ነብዩ ﷺ እንደገለፁት “ወንድምህን በሚጠላው ነገር ማውሳትህ ነው፡፡” “የማነሳው ነገር ከወንድሜ ዘንድ ካለስ?” ተብለው ሲጠየቁ “የምትለው ነገር ከወንድምህ ዘንድ ከኖረ በርግጥም አምተኸዋል፡፡ የምትለው ነገር ከሌለበት ግን በእርግጥም ቀጥፈህበታል” አሉ፡፡ [ሙስሊም የዘገቡት] አንዳንዱ ወንድሙን እያማ “ይሄ ከፊቱም የምናገረው ነው” ይላል፡፡ ይሄ ግን ሐቂቃውን አይቀይረውም፡፡ እንዲያውም ከፊቱ እየተናገረ ቅስሙን ሲሰብር ወይ ተጨማሪ ወንጀል ይደርባል፡፡ አለያ ደግሞ ተጣልቶ ፊትና ያቀጣጥላል፡፡ እንዲያውም አንዳንዱ “ይሄ ከፊቱም የምናገረው ነው” የሚለው ሃሜተኛ እንዳይባል ለአድማጮቹ የሚሰጠው ጉቦ ነው እንጂ ውሸቱን ነው የሚያወራው፡፡ ጉዳዩን ከሚታማው ሰው ዘንድ ቢያወራ እንኳን ከሰውየው ፊት በሚያወራው መልኩ አይሆንም፡፡
② የሃሜትን አስከፊነት መገንዘብ፡- አብዛሃኞቻችን ሃሜት ምን ያክል አስከፊ እንደሆነ በሚገባ አናውቅም፡፡ አንድ ሁለት ምሳሌ ብቻ ብንመለከት የጉዳዩን አስፈሪነት ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል፡፡
ምሳሌ አንድ፡- የመጀመሪያው ሃሜት ልክ የሞተ ወንድምን ስጋ እንደመብላት ነው የሚለው ቁርኣናዊ መልእክት ነው፡፡ ትኩረት ብንሰጠው ይሄ እጅግ ቀፋፊ ነገር ነው፡፡ እስኪ አስቡት አንድ ጨካኝ ገዢ “ሰዎችን በሃይል እየደበደበ የሞቱ ሰዎችን ስጋ እንዲበሉ አደረጋቸው” የሚል ዜና ከምስል ጋር ብንመለከት ምን ይሰማናል?! ሰቅጫጭ ነው አይደል?! የሆኑ ሰዎች የሰው ስጋ እየመተሩ፣ እየዘለዘሉ ሲበሉ ብንመለከትስ ምን ይሰማናል?! በቃ ጌታችንም ሃሜት ማለት የሞተ ወንድምን ስጋ እንመብላት ነው አለን፡፡ ሰው ባማን ቁጥር በአይነ ህሊናችን ጥርሳችን የተቦጫጨቀ የሰው ስጋ እንደያዘ ወይም እያኘከ እንደሆነ ብንስለው ዘግናኝ ምስል ይታየናል፡፡ ኢብኑ ዐባስ ረዲየላሁ ዐንሁ እንዲህ ይላሉ፡- “አላህ ይህን ምሳሌ የሰጠው የሞተን መመገብ አፀያፊ የሆነ ሐራም ስለሆነ ነው፡፡ ሃሜትም እንዲሁ በሃይማኖት የተወገዘ፣ ከነፍስ ዘንድ የሚያፀይፍ ነው፡፡”
ምሳሌ ሁለት፡- ነብዩ ﷺ እንዲህ ማለታቸው ነው፡፡ “በእርግጥም አንድ ሰው ደንታ ሳይሰጠው በተናገረው ንግግር ሰባ አመት ወደ ጀሀነም ይምዘገዘጋል!!” አልባኒ ሶሒሕ ብለውታል፡፡
ምሳሌ ሶስት፡- ነብዩ ﷺ በሁለት ቀብሮች ዘንድ አለፉ፡፡ ሰዎቹ በቀብራቸው ውስጥ የሚቀጡ ናቸው፡፡ “አንዱ ሰዎችን ያማ የነበረ ነው” አሉ፡፡ [ሶሒሑል ኣደብ አልሙፍረድ፡ 275]
እነዚህ ምሳሌ ብቻ ናቸው፡፡ ሌሎችም አስፈሪ መረጃዎችን አልፎ አልፎ ብንመልከትና ደዕዋዎችን ብናዳምጥ ጠቃሚ ነው፡፡
③ ለሃሜት የሚያጋልጡን መንገዶችን መለየት፡- በአብዛሀኛው ለሃሜት የሚያጋልጡን መንገዶች የሚከተሉት ናቸው፡-
ስራ መፍታት፡- ስራ ፈቶች በብዛት ሃሜተኞች ናቸው፡፡ እራሳችንን በስራ መጥመድ አንድ ከሃሜት መራቂያ ብልሃት ነው፡፡ ስለሆነም አእምሯችንን ስለሰዎች ከማሰብ ዞር በሚያደርጉን ስራዎች ላይ መጥመድ ፋይዳው ድርብርብ ነው፡፡ በተጨማሪም ቁርኣን በመቅራት፣ ዚክር በማድረግ፣ ጠቃሚ ፅሁፎችን በማንበብ፣ ሙሓዶራዎችን ወይም ደዕዋዎችን በማዳመጥ ትርፍ ጊዜያችን ከሃሜት በመራቅ በጠቃሚ ነገር ላይ ማሳለፍ እንችላለን፡፡ ዑለማዎቻችን እንደሚሉት ምላስ በጥሩ ነገር ካልጠመድናት ያለ ጥርጥር በመጥፎ ነገር መጠመዷ አይቀርም፡፡
ወሬ ማብዛት፡- ወሬው የበዛ ሰው ያለ ጥርጥር ለጥፋት የቀረበ ነው፡፡ ነብዩ ﷺ “ዝም ያለ ተረፈ” ይላሉ፡፡ ስለዚህ በዝምታ ውስጥ ያሉ ፋይዳዎችን ልናስተነትን ይገባል፡፡ ባጭሩ ወሬ መቀነሳችን ለሃሜት ከምንጋለጥባቸው መንገዶች ዋናውን መቀነስ ነው፡፡
የጓደኛ ጣጣ፡- መቼም ሃሜት የጋራ ወንጀል ነው፡፡ ሃሜት የሰማ ሰው በመቃወሙ የሚከተል አደጋ ካልኖረ በስተቀር መቃወም ግዴታው ነው፡፡ ይህን ያልቻለ ቢያንስ በልቡ ሊጠላ ይገባዋል፡፡ ያለበለዚያ አድማጩም እንደተናጋሪው ተጠያቂ ነው፡፡ መቼም እራሳችንም ሆንን ጓደኛችን በቀላሉ ነገሮችን ወደ ሃሜት የሚለውጥ አይጠፋም፡፡ ይህን ችግር አሰተውሎ ለህክምናው መታገል ብልሃት ነው፡፡ ችግሩ ከኛ ከሆነ ተቅዋን መላበስ ሁነኛ መፍተሄ ነው፡፡ ከጓደኞቻችንም ለዚህ ጥፋት የሚያጋልጡንን ከቻልን ግልፅ መመካከር ኖሮ ተያይዞ ከጥፋት በመራቅ ወደ ኸይር መጓዝ፡፡ ካልሆነ ግን በመራቅም ቢሆን ቢያንስ እራስን ከጥፋት ማትረፍ ትልቅ ብልሃት ነው፡፡ ይሄ ውሳኔ ለአንዳንዶቻችን ትልቅ መስዋእትነት ሊጠይቅ ቢችልም የሚከተለውን መዘዝ ማሰባችን ጉዳዩን ያቀለዋል፡፡
የልብ መድረቅ፡- እንዲያውም ቁልፉ እዚህ ላይ ነው፡፡ ስለዚህ ተቅዋችን ይጨምር ዘንድ ልንታገል ይገባል፡፡
④ ሙራቀባ (በእያንዳንዱ እንቅስቃሴያችን ላይ ዘወትር አላህን ማሰብ)፡- “ከሱ ዘንድ ረቂብና ዐቲድ ቢኖሩ እንጂ አንድም ንግግር አይናገርም” የሚለውን አስፈሪ ቁርኣናዊ መልእክት ማሰብ ጥሩ ነው፡፡
⑤ ነፍስን መቆጣርና መተሳሰብ፡- ህይወትን በግምት መግፋት አይገባም፡፡ ለራሳችን ከሐራም ነገሮች ያለንን ርቀት፣ ከግዴታ ነገሮች ያለንን መዘነጋት የምንገመግምበት ፋታ ልንሰጥ ይገባል፡፡ ካልሆነ ግን እራሳችንን ሳናስተውለው በቀላሉ ከማንመለስበት ርቀት ላይ ልናገኘው እንችላለን፡፡
⑥ የመልካም ቀደምቶችን አርአያ መከተል፡- ሌላው ከሃሜት መራቂያ ብልሃት ነው፡፡ በዚህ ረገድ የሰለፎች አቋም ምን ይመስል እንደነበር ተግባራዊ ተሞክሮዎችን ማጥናት ጠቃሚ ዘዴ ነው፡፡ ምን ያክል ሃሜትን ይፀየፉ እንደነበር፣ ለሃሜተኛ ምን አይነት መልስ ይሰጡ እንደነበር መመልከት፡፡ ይሄ ለሚያስተውል ሁሉ በራሱ ማንነት እንዲሸማቀቅ በማድረግ በተጨባጭ የሚታይ ውጤት የሚያስከትል ስለሆነ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ዘዴ ነው፡፡
⑦ ዱዓ፡- አላህ ምላሳችንን ከሃሜት እንዲጠብቅልን መማፀን አንዱ ከሃሜት መራቂያ መንገድ ነው፡፡
⑧ እውነተኛ ተውበት፡- ለምንፈፅመው የሃሜት ጥፋት እንዲሁ የዋዛ ፈዛዛ “አስተግፊሩላህ” ሳይሆን መስፈርት የሚያሟላ እውነተኛ ተውበት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ አንድ ሰው ያለ አግባብ የወሰደው የሰው ሐቅ ካለ በዚህ ጥፋቱ ከአላህ ፊት እንዳይጠየቅ የሚያስፈልጉ የተውበት መስፈርቶች አሉ፡፡ እነሱም
አንደኛ፡- አላህን ብቻ በማሰብ መመለስ- ኢኽላስ፡፡ አላህን አስቦ እስካልተመለሰ ድረስ ከጥፋቱ መራቁ ብቻውን ቀድሞ ከተፈፀመው ጥፋት ከመጠየቅ አያተርፈውም፡፡
ሁለተኛ፡- ስለፈፀመው ጥፋት መፀፀት (ጉዳዩን አቅልሎ ሊያይ አይገባምና)
ሶስተኛ፡- ከጥፋቱ ሙሉ ለሙሉ መራቅ (የሰው ሐቅ ካበት መመለስ)
አራተኛ፡- ዳግም ወደዚያ ጥፋት ላይመለስ ቁርጠኛ ውሳኔ ማድረግ
አምስተኛ፡- ተውበቱ የተውበት በር ባልተዘጋበት ጊዜ ውስጥ መደረጉ ነው፡፡
ከነዚህ መስፈርቶች አንዱን ያጓደለ ተውበቱ ትክክለኛ አይደለም፡፡ ይህንን መነሻ በማድረግ ሃሜት ላይ በወደቅን ቁጥር እውነተኛ የሆነን ተውበት ብናደርግ በቀጣይ ተመሳሳይ ጣጣ ውስጥ ላለመግባት እንጠነቀቃለን፡፡
⑨ ከወንድም ክብር ላይ መከላከል ያለውን ፋይዳ ማሰብ፡- ወንድምህ ሲታማ ከሱ መከላከልህ ላንተ ትልቅ ሽልማት አለው፡፡ ነብዩ ﷺ “ከወንድሙ ክብር ላይ የተከላከለ አላህ በቂያማ ቀን ከፊቱ እሳትን ያርቅለታል” ይላሉ፡፡ ስለዚህ ይሄ ሽልማት እንዳያመልጥህ ከወንድምህ ተከላከል፡፡ አንድ ሽልማት፡፡ ይሄ ተግባርህ ሃሜት ላይ የሚወድቅ ወንድምህንም ከጥፋት ስለሚያቅበው ሌላም ሽልማት አለህ፡፡ ያለበለዚያ ግን ከአፍታ በኋላ እራስህን የሃሜቱ አካል ሆነህ ልታገኘው ትችላለህ፡፡
①∅ ሆደ ሰፊ መሆን፡- ለሃሜት ከሚገፉን ነገሮች አንዱ በሌሎች ላይ የሚኖረን ቅሬታ ነው፡፡ ታጋሽና ይቅር ባይ ብንሆን ግን ስለሰዎች ክፉ እንዳናስብና በክፉ እንዳናነሳቸው ይረዳናል፡፡
①① ሃሜት የሚፈቀድባቸውን ሁኔታዎች ጠንቅቆ መለየት፡- የሰዎችን ድክመት ወይም ጥፋት መናገር የሚፈቀድባቸው ወይም ግዴታ የሚሆንባቸው ውስን ሁኔታዎች እንዳሉ የሚታወቅ ነው፡፡ እነዚያ ሁኔታዎች ለአስገዳጅ ምክንያት ብቻ የሚፈቀዱ ስለሆነ ያለ አግባብ እየመነዘርናቸው እንዳይሆን መጠንቀቅ አንዱ ከሃሜት መራቂያ ስልት ነው፡፡ አንዳንዱ በሸሪዐዊ ምክንያቶች አስታኮ የግል ቂሙን የሚያወራርድ፣ ተያያዥነት በሌላቸው ግለሰባዊ ጉዳዮች ውስጥ ዘልቆ የሚገባ፣ አልፎም እንደ አካላዊ ቅርፅ፣ ብሄር፣ ቋንቋ፣ ወዘተ ያሉ የፈጣሪ ስጦታዎችን ሳይቀር እያነሳ የሚያንቋሽሽ ያጋጥማል፡፡ ለዚህ አይነቱ ጥፋት እራስን መሸወድ ካልሆነ በስተቀር ሃሜት የሚፈቀድባቸውን ሁኔታዎች ማጣቀስ አያዋጣም፡፡ የአላህ ሶላትና ሰላም በነብያችን ላይ ይሁን።
(ኢብኑ ሙነወር፣ ታህሳስ 20/2009)