Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

የሱንናው አንበሳ


....የሱንናው አንበሳ.....
ሸይኽ ሙሐመድ ሰዒድ ረስላን ከግብፁ ዋና ከተማ ካይሮ 45 ደቂቃ ርቀት ላይ በምትገኘው መኑፍያ መንደር እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ኖቬምበር 23, 1955 ተወለዱ። የቀደምት ደጋግ ትውልዶችን (ሰለፎችን) በመከተል የሚታወቁት እኒህ ግብፃዊ ሰለፊይ ዓሊም ከአል–አዝሀር ዩኒቨርሲቲ በህክምና(Medicine) ዲግሪ እንዲሁም በቀዶ ጥገና(Surgery) ዲግሪያቸውን ተቀብለዋል። በተጨማሪም ከዚያው ዩኒቨርሲቲ የኢስላማዊ ጥናት ትምህርት ክፍል(Department of Islamic studies) በዓረብኛ ቋንቋ ዲግሪ እንዲሁም "ضوابط الرواية عند المحدثين" በሚል ጥናት በከፍተኛ ማዕረግ ማስትሬት ዲግሪያቸውን(Master's) በሐዲስ ዘርፍ አግኝተዋል። ስድስቱን የሐዲስ ዘጋቢዎች በማጥናት አሁንም በከፍተኛ ማዕረግ በሐዲስ Ph.D ዓለም አቀፍ ሰርተፍኬት ወስደዋል። በተጨማሪም ሸይኹ ሰንሰለታቸው እስከነቢዩ ሶለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም የሚደርስ "الأربعين البلدانية" ብለው የሰየሟቸውን የ40 ሐዲሶች ሰነድ ኢጃዛ በክብር አግኝተዋል።
ሸይኽ ረስላን ላይ ተፅዕኖ ከፈጠሩ ታላላቅ ዓሊሞች መካከል ሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚያና ተማሪያቸው ኢማም ኢብኑል ቀይም እንዲሁም ከግብፅ ታዋቂ ዓሊሞች መካከል ኢማም ማሕሙድ ሻኪርና ወንድማቸው ኢማም አሕመድ ሙሐመድ ሻኪር ይገኙበታል።
ሸይኽ ረስላን መነሻውን ሀገራቸው ካደረገው ኢኽዋነል ሙስሊሚን (Muslim Brotherhood) በማስጠንቀቅ በስፋት ይታወቃሉ። የአንጃውንና መሪዎቹን አደገኛና ጠማማ አካሄድ በመረጃ እያወጡ በማጋለጥ እንዲሁም ዲሞክራሲንና ፖለቲካ ፓርቲዎችን በማውገዝ ረጅም አመታትን አሳልፈዋል። በሙስሊም መንግስታትና መሪዎች ላይ አምፆ መውጣትን የሚቃወሙት ሸይኽ ረስላን እውነትን ወደሗላ ሳይሉና የወቃሽን ወቀሳ ሳይፈሩ ይናገራሉ። በተውሒድና ሱንና ላይ ያላቸውን ጠንካራ አቋም ያዩት ታላቁ ዓሊም ሸይኽ ረቢዕ "የሱንና አንበሳ"(أسد السنة) በማለት አሞካሽተዋቸዋል። ህይወታቸውን በዛሂድነት የሚመሯት ሸይኹ በመልካም ስነምግባራቸው ይታወቃሉ።
ባሉበት መስጅድ ከ4000 (አራት ሺ) በላይ ተማሪዎች ያሏቸው ሲሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ ከአሜሪካ፣ ጃፓን፣ ፈረንሳይ፣ ስፔን፣ እንግሊዝ፣ ካዛኪስታን፣ ሩሲያና ከሌሎች በርካታ ሀገራት በሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች አሏቸው። በተለያዩ ርዕሶች ዙሪያ በርካታ ንግግሮችና ፅሁፎችን ለሙስሊሙ አበርክተዋል።
አላህ የሞቱትን ይቅር ብሎ በህይወት ላሉ ዓሊሞቻችን በሐቅ ላይ ፅናቱን እንዲሰጣቸውና ተተኪዎቻቸውንም እንዲያበዛ እንለምነዋለን።
(ያሲን ፈየሞ ፣ ጥቅምት 2008)

Post a Comment

0 Comments