Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

እንቶ ፈንቶ ወሬዎችን ከማሰራጨት እንቆጠብ!




እንቶ ፈንቶ ወሬዎችን ከማሰራጨት እንቆጠብ!
ዛሬ አንድ መስጂድ ውስጥ ይህን ከስር የምትመለከቱትን ፅሁፍ ሲያሰራጩ ነበር፡፡ ይህን ፅሁፍ ብዙዎቻችን እንደምናውቀው እገምታለሁ፡፡ ለበርካታ አመታት በተለያዩ ቋንቋዎች እየተረጎሙ እያሰራጩት ነው፡፡ መዘንጋት የሌለበት ነገር ግን
1. ዲናችን የትኛውንም እምነታዊ ጉዳይ ያለማስረጃ ማስተናገድን አይፈቅድም፡፡ ይህን መልእክት አስተላለፈ የተባለው ሰውየ ማንነት በትክክል አይታወቅም፡፡ ሰውየው ቢታወቅ እንኳን በትክክል የሱ ንግግር መሆኑን ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡
2. ይህን መልእክት ስላስተላለፈ ብቻ አንድ ሰው የነብዩን ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ሸፈዐህ ይታደላል ማለት ያለ እውቀት መናገር ነው፡፡ ዲናችን ጥንት ነው የተሟላ የሆነው፡፡ በድርዮች ሶሐብዮች የማያውቁት ነገር ዛሬ ተነስቶ ዲን አይሆንም፡፡ ነብዩም ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም “የኛ ትእዛዝ የሌለበትን ስራ የሰራ እሱ (ስራው) ተመላሽ ነው (ውድቅ ነው)” ብለዋል፡፡
3. በዚህ ኹራፋ ውስጥ እንዲህ የሚል መልእክት አለ፡ “ይህ ደብዳቤ የደረሰው ሰው ቢያንስ ከ20 እስከ 40 ኮፒ እያባዛችሁ አሰራጩ፡፡ ይህን ያደረገ ሰው አላህ የነብያችንን ውዴታ ሙሃባ ያገኛል፡፡ እንዲሁም ያቀደው ያሰበው ሁሉ ይሳካለታል፡፡ ከዚህ በፊት አይቶ የማያውቀውን ነገር ማየት ይጀምራል፡፡” ይሄ አይን ያወጣ ቅጥፈት ነው፡፡ አንድን ከማስረጃ ጋር የተኳረፈ እንቶ ፈንቶ ያሰራጨ ሰው አይደለም ይህን ሁሉ ሊያገኝ ቀርቶ ይልቁንም ባለማወቁ ካልተረፈ በስተቀር ከአላህ ፊት ተጠያቂ ነው የሚሆነው፡፡ ምክንያቱም በዲን ስም ዲንን የሚበክል ነገር እየፈፀመ፣ ሰዎችን እያታለለ ነውና፡፡
4. ደብዳቤው ውስጥ “አንድ ክሌቨርን የሚባል ሰው ይህ ደብዳቤ ደርሶት በማባዛት አሰራጭቶ ከትንሽ ቀኖች በኋላ ለዚህ ሰውየ ብዙ ጥሩ እድል ገጠመው፣ አብዱሰላም የተባለ ሰውዬ ይህ ደብዳቤ ደርሶት ችላ በማለቱ ከተወሰኑ ቀኖች በኋላ ከሚሰራው ስራ ተፈናቅሏል፣…” ጥያቄ ለመሆኑ እነዚህ ሰዎች ያገኙትን ያገኙት ወይም የደረሰባቸው ነገር የደረሰባቸው በዚህ ምክንያት መሆኑን በምን አረጋገጠ፡፡ ይሄ ሱፍዮች የዋሆች ላይ የሚፈፅሙት አይነት ባዶ ማስፈራሪያ ነው፡፡ ከነሱ ጋር የተጋጨ የሆነ ሰው የሆነ አደጋ ካጋጠመው አደጋውን እነሱ እንዳደረሱት ይጎረራሉ፡፡ ይሄ በማስረጃ የማሳመን አቅሙ የሚቀላቸው ሰዎች የሚፈፅሙት ባዶ ውዥንብር ነው፡፡
5. በመጨረሻም ሰውየው ፅሁፉን አባዝታችሁ ለሌላ አሰራጩ እያለ በአላህ ስም ይማፀናል፡፡ እውነት ሙስሊም ከሆነ ይህን የሚሰራው አላህ ሂዳያ ይስጠው፡፡ ሙስሊም ከሆነ ማለቴ ከሃዲዎችም ጊዜ እየጠበቁ እንዲህ አይነት ኹራፋቶችን በማሰራጨት ሙስሊሙን ባልባሌ ነገር እያዘናጉ፣ በሂደትም እምነቱን እየሸረሽሩ ስለሆነ ነው፡፡ እናም ወንድም እህቶች ከዚህም ይሁን መሰል እንቶ ፈንቶ ወሬዎች እራሳችንን ልናቅብ ሌሎችንም ልናስጠነቀቅ ይገባናል፡፡ ከፅሁፋቸው መሀል የባል ሐቅ ስለመጠበቅ፣ ስለሶላት፣ ፆም፣ ዘካ፣ ሐጅ፣ ሰኞና ሐሙስ መፆም የመሳሰሉትን መጥቀሳቸው ሊሸውደን አይገባም፡፡ እነዚህን ነገሮች ከህልም ወይም ከኹራፋት ሳይሆን ከቁርኣንና ከሐዲሥ ነው የወሰድናቸው፡፡ እንቶ ፈንቶ የሚያራግብ ሁሉ ከመሀል ላይ የሆነ ሸሪዐዊ ነገር ስለሰነቀረ ብቻ የምናምነው ከሆነ ከዲናችን ምን ይቀረናል? በዲናችን ጉዳይ በጣም ጠንቃቃ ልንሆን የግድ ይለናል፡፡ ከዚህ በተረፈ ይሄ ዲን ነው ከማን እንደምንወስደው ልንለይ ይገባል፡፡ ታላቁ ታቢዒይ ሙሐመድ ኢብኑ ሲሪን ረሒመሁላህ “ይሄ እውቀት ዲን ነው፡፡ ዲናችሁን (ኢስላማዊ እውቀታችሁን) ከማን እንደምትወስዱ አስተውሉ” ይሉናል፡፡
ወስሰላም
(ኢብኑ ሙነወር፣ ነሀሴ 1/2007)

Post a Comment

0 Comments