Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

የሀረሩ የዒልም ተራራ! ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ ረሒመሁላህ



የሀረሩ የዒልም ተራራ!
ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ ረሒመሁላህ

ሙሉ ስማቸው ሸይኽ ሙሐመድ አማን ኢብኑ ዐልይ አልጃሚ ሲሆኑ በ 1349 ዓ.ሂ. በሀረር ጨርጨር ተወለዱ፡፡ የዒልም ጉዟቸውን ገና ልጅ እያሉ ቁርኣንን በመቅራት የጀመሩት ሲሆን በተጨማሪም የዐረብኛ ቋንቋን እና ፊቅህን እዚሁ ኢትየጵያ ውስጥ ተምረዋል፡፡ ይሁን እንጂ የዒልም ጥማታቸው እትብታቸው ከተቀበረበት ሀገር ቢያስወጣቸው በሶማሊያ አድርገው ብዙ ፈተናና እንግልት አስተናግደው በዔደን ብለው ሑደይዳህ ደረሱ፣ የመን፡፡ ረመዳንን እዚያው ፆመው ከዚያም ወደ ሷሚጧህ ደቡብ ሰዑዲ ዐረቢያ አቀኑ፡፡ ከዚያም በእግራቸው ጉዟቸውን ቀጥለው መካ ገብተው ሐጅ አደረጉ፡፡ መካ ሳሉም ከሸይኽ ኢብኑ ባዝ ጋር ተዋወቁ፡፡ አብረዋቸውም ወደ ሪያድ ተጓዙ፡፡
ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ:- ከሪያድ የዒልም ተቋም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ጨርሰዋል፡፡ ከሸሪዐ ፋኩልቲ በኢንቲሳብ ተመርቀዋል፡፡ በፓኪስታን ከፑንጃብ ዩኒቨርሲቲ ማስትሬታቸውን ተቀብለዋል፡፡ በካይሮ ዳሩልዑሉም ዶክትሬታቸውን ሰርተዋል፡፡
ሸይኽ ሙሐመድ አማን ታላላቅ ዑለማዎች ዘንድ እጅጉን የተከበሩና የታመኑ ነበሩ፡፡ ሪያድ ላይ ተማሪ በነበሩበት ጊዜ ኢብኑ ባዝ ዘንድ ታማኝ ከመሆናቸው የተነሳ በጊዜው ወደነበሩት ሙፍቲ ሸይኽ ሙሐመድ ኢብራሂም አቅርበዋቸው በጃዛን ክልል የሷሚጧ የእውቀት ማእከል ውስጥ አስተማሪ ሆነው ተመድበዋል፡፡ የመዲና ኢስላማዊ ዩኒቨርሲቲ ሲከፈት በሸይኽ ኢብኑ ባዝ ተመርጠው በዩኒቨርሲቲው ስር በነበረው ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የአቂዳህ አስተማሪ ሆነው አገልግለዋል፡፡ ኋላም በዩኒቨርሲቲው የሸሪዐህ ኮሌጅ ውስጥ አስተማሪ ሆነው አገልግለዋል፡፡ በመስጂደንነበዊ ውስጥም ዘወትር ያስተምሩ ነበር፡፡
ሸይኾቻቸው
ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ ረሒመሁላህ በሁለቱ ታላላቅ የሰዑዲያህ ሙፍቲዎች በሸይኽ ሙሐመድ ኢብኑ ኢብራሂም እና ሸይኽ ዐብዱልዐዚዝ ኢብኑ ባዝ ላይ ተምረዋል፣ ሁሉንም አላህ ይማራቸውና፡፡ በተጨማሪም ታላቁ የቁርኣን ሙፈሲር ሙሐመድ አሚን አሽሸንቂጢ፣ ሙሐዲሥ ሐማድ አልአንሷሪ፣ ሸይኽ ዐብዱርረዛቅ አልዐፊፊ፣ ሸይኽ ሙሐመድ ኸሊል ሀራስ፣ ሸይኽ ዐብደላህ አልቀርዓዊ ላይ ተምረዋል፡፡ እነዚህ ማለት በአሁኑ ሰአት ያሉ አለም አቀፍ እውቅና ያላቸው ዑለማዎችን ያፈሩ ማስተዋወቅ የማይሹ ስማቸው ከሩቅ የሚያበራ የዒልም ከዋክብት ናቸው፡፡ እነዚህ ናቸው የሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ ሸይኾች፡፡
ተማሪዎቻቸው፡-
አልጃሚ በሪያድ፣ ጃዛን፣ ጂዳህ፣ መዲናህ፣ ፓኪስታን፣ ግብፅና ሌሎችም የአፍሪካ ሀገራት በተዘዋወሩበት ያስተማሯቸው እጅግ ብዙ ስለሆኑ ተማሪዎቻቸውን መዘርዘር ይከብዳል፡፡ ባይሆን በጣም የጎሉትን ብቻ ጥቂት እናንሳ፡፡ ሸይኽ ረቢዕ ኢብኑ ሃዲ አልመድኸሊ፣ ሸይኽ ዘይድ ኢብኑ ሃዲ አልመድኸሊ፣ ሸይኽ ዐልይ ኢብኑ ናሲር አልፈቂሂ (በመስጂደንነበዊ አስተማሪ)፣ ሸይኽ ሙሐመድ ሐሙድ አልዋኢሊ (በመስጂደንነበዊ አስተማሪ እና በጃሚዐቱልኢስላሚያህ የከፍተኛ ትምህርት ወኪል)፣ ሸይኽ ፈላህ ሙንደካር (በኩወይት ዩኒቨርሲቲ አስተማሪ)፣ ሸይኽ ሷሊሕ ኢብኑ ሰዕድ አስሱሐይሚ እና ሌሎችም፡፡
ኪታቦቻቸው፡-
الصفات الإلهية في الكتاب والسنَّة النبوية في ضوء الإثبات والتنـزيه، منـزلة السنَّة في التشريع الإسلامي، مجموع رسائل الجامي في العقيدة والسنَّة، العقيدة الإسلامية وتاريخها، حقيقة الديموقراطية وأنها ليست من الإسلام، حقيقة الشورى في الإسلام، أضواء على طريق الدعوة إلى الإسلام، تصحيح المفاهيم في جوانب من العقيدة، المحاضرة الدفاعية عن السنة المحمدية، العقل والنقل عند ابن رشد، طريقة الإسلام في التربية، مشاكل الدعوة والدعاة في العصر الحديث، الإسلام في أفريقيا عبر التاريخ
ባህሪያቸው
በጣም ቁጥብ፣ ከሰው ጋር መቀላቀል የማያበዙ እና ጊዜያቸውን ባግባቡ ይጠቀሙ ነበሩ፡፡ ሸይኹ ሲበዛ ይቅር ባይ ነበሩ፡፡ ስማቸውን ያጎደፉ ሰዎች መጥተው ይቅርታ ሲጠይቋቸው “በኔ ሰበብ አላህ አንድንም እሳት እንዳያስገባ እከጅላለሁ” እያሉ ይቅርታ ያደርጉ ነበር፡፡ እንዳውም “እኔ ዘንድ መምጣትም አያስፈልግም፡፡ እኔ ሁሉንም ይቅር ብያለሁ” ይሉ ነበር፡፡ አብረዋቸው ላሉም ይህን እንዲያደርሱላቸው ይጠይቁ ነበር፡፡
በመጨረሻም ሸይኹ ለአንድ አመት ያክል በህመም ከተሰቃዩ በኋላ በ 1416 አመተ ሂጅራ ከዚች ዐለም በሞት ተለዩ ረሒመሁላሁ ተዓላ፡፡ ሸይኽ ሙሐመድ አማን ለ 40 አመታት ተውሒድን ያስተማሩ ታጋይ ናቸው፡፡ ሸይኹ የመጨረሻ ጣእረ-ሞት ላይ እንኳን ሆነው “ዐቂዳ፣ ዐቂዳ” እያሉ የዐቂዳን ነገር አደራ እያሉ ነው የሞቱት፡፡
ሸይኽ ሙሐመድ አማን ረሒመሁላህ በታላላቅ ዑለማዎች አንደበት
1. ሸይኽ ሐማድ አልአንሷሪ ረሒመሁላህ ሙሐመድ አማን አልጃሚን “ኡስታዝ” እያሉ ይጠሯቸው ነበር እሳቸው ለሸይኽ ሙሐመድ አማን ጃሚ ሸይኽ ከመሆናቸው ጋር፡፡
2. ኢብኑ ባዝ ስለ ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ እንዲህ ይላሉ፡- “እኔ ዘንድ በእውቀቱ፣ በታላቅነቱ፣ በጤናማ ዐቂዳው፣ ወደ አላህ ሱብሓነሁ ወተዓላ መንገድ በመጣራት ላይ እና ከቢድዐ እና ከኹራፋት በማስጠንቀቅ ላይ ንቁ በመሆኑ የታወቀ ነው፡፡ አላህ ይማረው፡፡ ከሰፊ ጀነቱ ውስጥም ያኑረው፡፡ ዘሮቹንም ያሳምርለት፡፡ እኛንም እናንተንም እሱንም በተከበረ ሃገሩ (በጀነት አላህ) ያሰባስበን፡፡ እሱ ሰሚና ቅርብ ነው፡፡” “ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ እና ሸይኽ ረቢዕ አልመድኸሊ ሁለቱም ከአህሉስሱናህ ናቸው፡፡ እኔ ዘንድም በእውቀት፣ በታላቅነት እና በጤናማ ዐቂዳ ነው የሚታወቁት” ይላሉ፡፡ ሌላ ጊዜም በዱዐቶች መካከል ስላለ አለመግባባት አንስተው ጠቅለል ያለ ምክር ሲሰጡ አንዳንዶች መንካት የፈለጉት እነ ሸይኽ ሙሐመድ አማን ጃሚን፣ እነ ሸይኽ ረቢዕ፣ በጥቅሉ የመዲና ዑለማዎችን ነው ብለው አወሩ አስወሩም፡፡ ኋላ ላይ “በሰጣችሁት ምክር ላይ መንካት የፈለጋችሁት የተወሰኑ የመዲና ዑለማዎችን እና መሻኢኾችን ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚን፣ ሸይኽ ረቢዕ አልመድኸሊን፣ ሸይኽ ሷሊሕ አስሱሐይሚን፣ ሸይኽ ሷሊሕ አልዐቡድ… እየተባለ እየተወራ ነው ተብለው ሲጠየቁ የሰጡት መልስ ባጭሩ ይህን ይመስል ነበር፡- “… በመግለጫችን ማንንም በተናጠል እንዳላሰብን በተደጋጋሚ ገልፀናል፡፡ የፈለግነው ባጠቃላይ በሀገር ውስጥም በውጭም ላሉ ምክር ነው፡፡ የጠቀሳችኋቸው ስሞች ምርጥ ከሆኑ ወንድሞቻችን፣ ከሱናህ ዑለማዎች ናቸው፡፡ እኛ ዘንድም በትክክለኛ አካሄዳቸው፣ በመልካም ዝናቸው፣ በጤናማ ዐቂዳቸው እና ወደ አላህ ዐዘ ወጀል በመጣራታቸው ከታወቁት ውስጥ ናቸው፡፡..” በድጋሚ “አሁን ስማቸው በተዘረዘሩት መሻኢኾች ላይ ያላችሁ አስተያየት ምንድን ነው? ወጣቶችን እና እውቀት ፈላጊዎችን ከነዚህ እንዲጠቀሙ ትመክራላችሁ?...” ሲባሉ “በነሱ ላይ ያለንን አስተያየት ግልፅ አደረግን እኮ፡፡ እነሱ ምርጥ ከሆኑ ወንድሞቻችን፣ ከዑለማኡስሱናህ ናቸው፡፡ ከነሱ እውቀትን በመውሰድ እመክራለሁ” አሉ፡፡
3. ሸይኽ ዐብዱልሙሕሲን አልዐባድ፡- “ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚን በሪያድ የዒልም ማእከል ተማሪ ሳለ ከዚያም በመዲና ኢስላማዊ ዩኒቨርሲቲ ሁለተኛ ደረጃ ላይ አስተማሪ ሳለ፣ ከዚያም ዩኒቨርሲቲው ውስጥ ሲያስተምር አውቀዋለሁ፡፡ ሳውቀው ያማረ ዐቂዳ፣ ጤነኛ አካሄድ ያለው ነው፡፡ በሰለፎች አካሄድ መሰረት ዐቂዳን ግልፅ ማድረግ ላይ፣ ከቢድዐዎች ማስጠንቀቅ ላይ ያተኩር ነበር፡፡ ይህም በትምህርቶቹ፣ በሙሐዶራዎቹ፣ በኪታቦቹ ነበር፡፡ አላህ ይማረው፣ ይዘንለት ምንዳውንም ያብዛለት፡፡”
4. ሸይኽ ሷሊሕ አልሉሐይዳን፡ “ሙሐመድ አማን አልጃሚ ጥሩ ሰው ነው፡፡ ዐቂዳውም የሰለፊ አቂዳ ነው፡፡”
5. ሸይኽ ረቢዕ ኢብኑ ሃዲ አልመድኸሊ፡- “ሸይኽ ሙሐመድ አማን ረሒመሁላህ ሙእሚን፣ ሙወሒድ፣ ሰለፊ፣ ዲኑን አዋቂ፣ በዐቂዳህ እውቀት ላይ ብቃት ያለው ሰው እንደሆነ ነው እኔ ከሱ የማውቀው፡፡ ዐቂዳን በማቅረብ በኩል እንደሱ የተካነ ሰው አላየሁም፡፡…”
6. ሸይኽ ዑመር ሙሐመድ ፈላታህ፡- መዲና በነብዩ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም መስጂድ ውስጥ አስተማሪ የነበሩና የዳሩልሐዲሥ ተቋም ስራ አስኪያጅ የነበሩ ናቸው- ስለ ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ እንዲህ ይላሉ፡- “በጥቅሉ ሸይኹ ረሒመሁላህ እውነት ተናጋሪ፣ ጠንካራ የአህሉስ-ሱናህ ተከታይ፣ ጠንካራ ሞራል ያለው፣ በቃላትም በተግባርም ወደ አላህ የሚጣራ፣ ካልባሌ ነገሮች ምላሱ የተቆጠበ፣ አንደበተ-ርቱእ፣ የአላህ ህግጋት ሲጣሱ ፈጥኖ የሚቆጣ ሰው ነበር፡፡ በነብዩ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም መስጂድ ይሰጠው የነበረው ትምህርቱ፣ ያሳተማቸው ኪታቦቹ፣ ለደዕዋ ያደረጋቸው ጉዞዎቹ ስለሱ ያወራሉ፡፡ አብሬው ተጉዣለሁ፡፡ ምን ያማረ ጓደኛ ነበር! የ“አድዋኡልበያን” ተፍሲር ባለቤት (ሸይኽ ሙሐመድ አሚን አሽ-ሺንቂጢ) ጋር አብሮ ተጉዟል፡፡ ለሱም ምን ያማረ ጓደኛ ነበር፡፡ የሰዎችን ማንነት አጉልቶ ለማሳየት ጉዞ ትልቅ ሚና እንዳለው ይታወቅ፡፡ ሙሐመድ አማን ጥፋት ካየ ላለማስከፋት ብሎ መመሳሰል አያውቅም፡፡ መደባበቅ አይሆንለትም፡፡ አይሟገትም፣ አይከራከርም፡፡ ማስረጃ ካለው በግልፅ ያወጣዋል፡፡ ሐቅ በሌላኛው ወገን እንደሆነ ካስተዋለ ሳያመነታ ከነበረው አቋሙ ይመለሳል፡፡ ይህ ነው የሙእሚኖች ባህሪ! አላህ እንዲህ ሲል እንደገለፀው ((ወደ አላህና ወደ መልእክተኛው በመካከላቸው እንዲፈርዱ በተጠሩ ጊዜ የሙእሚኖች ቃል ሊሆን የሚገባው “ሰምተናል፣ እንታዘዛለን” ማለት ነው፡፡ እነዚህ ስኬታማዎቹ ናቸው፡፡)) (አን-ኑር፡ 51)
አላህ ምስክሬ ነው ኢስላምን በማገልገል በኩል ያለበትን አደራ በብዛት ተወጥቷል፡፡ የነብዩን ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ሱና አሰራጭቷል፡፡ ብዙ ፈተና፣ ብዙ ተንኮልና ሴራ ደርሶበታል፡፡ ግና አልታጠፈም፡፡ ጌታውን እስከሚገናኝ ድረስ አልደነገጠም፡፡ የመጨረሻ ቃሉ ላኢላሀኢለላህ ሙሐመዱን ረሱሉላህ የምትለዋ ምስክርነት ሆናለች፡፡”
7. እኔ እራሴ በጆሮዬ የሰማሁት ምስክርነት፡- የመዲና ዩኒቨርሲቲ ከመጀመሪያዎቹ ምሩቆች አንዱ የሆኑት ኢትዮጵያዊው ሸይኽ ሙሐመድ ሐሰን ሙሐመድኑር ረሒመሁላህ (ባለፈው ረመዳን ነው የሞቱት) መዲናህ ውስጥ በሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ ከተማሩ ተማሪዎች አንዱ ናቸው፡፡ ወላሂ! በእውቀታቸውም በአቀራረባቸውም የተዋጣላቸው እንደነበሩ ደግመው ደጋግመው ሲያደንቋቸው በጆሮየ ሰምቻለሁ፡፡ ስለሳቸው ወሬ ሲነሳ ሞቅ አድርገው በስሜት ተመስጠው ነበር የሚያወሩት፡፡ “ፈትፍቶ እኮ ነበር የሚያጎርሰው” እያሉ የአቀራረብ ችሎታቸውን ሲያወድሱ አይረሳኝም፡፡ ሁለቱንም አላህ ይማራቸው፡፡
እኚህ ናቸው እንግዲህ ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ ረሒመሁላህ ዑለማዎቹ ዘንድ፡፡ እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ “ለዑለማእ ክብር እንቆረቆራለን” በሚሉ አስመሳዮች ብዙ ተወንጅለዋል፣ ዛሬም እየተወነጀሉ ነው፡፡ ለመሆኑ ሸይኽ ሙሐመድ አማን ልክ አዲስ አንጃ እንደመሰረቱ የሚያናፍሱባቸው፣ በመጥፎ የሚያነሷቸው ሰዎች እነማን ናቸው? መልሱ ከታላላቅ ዑለማዎች ዘንድ አለ፡፡ ይሄውና
1. ሸይኽ ሙሐመድ አስሱበይዪል፡- “እንደ ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ እና ሸይኽ ረቢዕ ኢብኑ ሃዲ አልመድኸሊ ያሉ መሸኢኾችን ካሴቶች ለሚከለክሉ ሰዎች ምን ይመክራሉ? የሸይኽ ረቢዕ ካሴቶች ፊትና ይፈጥራሉ በሚል መንሰኤ ነው” ተብለው ሲጠየቁ እንዲህ ብለው ነበር የመለሱት፡- “አዑዙ ቢላህ! አዑዙ ቢላህ! የነዚህ ሸይኾች ካሴቶች እጅግ ጥሩ ከሆኑ ካሴቶች ናቸው፡፡ እነዚህ ወደ ሱና ነው የሚጣሩት፣ ሱናን አጥብቆ ወደመያዝ፡፡ በነዚህ ላይ የስሜት ተከታይ የሆነ ሰው ካልሆነ በስተቀር በክፉ አይናገርም፡፡ በነዚህ ላይ ከሚናገሩት አብዛሀኞቹ ሒዝቢዮች (ቡድንተኞች) ናቸው፡፡ እነዚያ ለሆነ ቡድን እራሳቸውን የሚያስጠጉ የሆኑት፡፡ …”
2. ሸይኽ ፈውዛን፡- “ጃሚያ የሚለውን ቅፅል የፈጠሩት ሒዝቢዮች ናቸው፡፡ እናም እራስህን ከሙናፊቆች ተራ አታሰልፍ፡፡ እነዚያ የሙእሚኖችን ህብረት የለያዩ የሆኑት፡፡” “ሙሐመድ አማን አልጃሚ ወንድማችን እና ጓደኛችን ነው፡፡ ከዚች ከተባረከች ዩኒቨርሲቲ ተመርቆ ወደ ኢስላማዊ (የመዲና) ዩኒቨርሲቲ እና ወደ መስጂደንነበዊ አስተማሪ ሆነ ሄደ፡፡ ወደ አላህ ተጣሪ ነበር፡፡ ከሱ ኸይር እንጂ ሌላ አናውቅም፡፡ ጃሚያ የሚባል ቡድንም የለም!! ይሄ ቅጥፈትና ስም ማጥፋት ነው፡፡ … ነገር ግን ወደ ተውሒድ ስለሚጣራ፣ ከቢድዐና ፈር ከለቀቁ አስተሳሰቦችም ስለሚከለክል ጠላት ያደርጉታል፣ በዚህ ቅፅልም ይጠሩታል፡፡” “ጃሚያ የሚባል ቡድን የለም፡፡ ጃሚያ የሚባል ቡድን የለም፡፡ ሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ ረሒመሁላህ እናውቀዋለን፡፡ ከአህሉስሱናህ ወልጀማዐህ ነው፡፡ ወደ አላህ ዐዘ ወጀል ነው የሚጣራው፡፡ ቢድዐ ይዞ አልመጣም፡፡ ምንም አዲስ ነገር አላመጣም፡፡ ነገር ግን ለዚህ የገፋፋቸው ለዚህ ሰውየ ያላቸው ጥላቻ ነው፡፡ ልክ ሸይኽ ሙሐመድ ኢብኑ ዐብዲልወሃብ ወደ ተውሒድና ዒባዳን ለአላህ ብቻ ወደ ማጥራት በተጣራ ጊዜ ከስሙ ጋር አያይዘው ወሃብያ እንዳሉት እሱንም ከስሙ ወስደው ጃሚያ የሚባል ቡድን እንዳለ ያቀርባሉ፡፡ ይሄ የተንኮል ሰዎች ባህሪ ነው፡፡ … ምቀኝነት ነው አንዳንዱን ለዚህ የሚያደርሰው፡፡ ሁሉም የሚናገረውን ይሸከማል፡፡”
3. ሸይኽ ዐብዱልሙሕሲን አልዐባድ፡ “ጃሚያህ የሚለው ሱናን አጥብቀው የያዙ ሰዎችን ከነሱ ለማስበርገግ የሚጠቀሙት መጤ ቃል ነው፡፡ ወሃቢ ከሚለው ጋር ተመሳሳይ ነው፣ ሰዎችን ከነሱ ለማራቅ ነው፡፡”
4. ሸይኽ ዐብዱልሙሕሲን አልዑበይካን፡- ሙሐመድ አማን አልጃሚ ረሒመሁላህ የተከበረ ዐሊም ነው፡፡ በአላህ ይሁንብኝ እሱን በመጥፎ የሚያነሱት ሰዎች እውቀቱን፣ በተቅዋ የታጀበ ጥንቃቄውን፣ እውነተኛነቱን ያውቃሉ፡፡ ነገር ግን በማይፈልጉት መጥቶባቸዋል፡፡ ስልጣን ላይ ለመድረስ በማሰብ አብዮት ለመቀስቀስ አስበው ሰዎችን በመሪዎች ላይ ለማነሳሳት የገነቡትን ከንቱ የሆነ አካሄድ ከመሰረቱ ንዶባቸዋል፡፡ ይህን ቆሻሻ አካሄዳቸውን የሚንድባቸው ሲመጣ አሴሩበት፡፡ ውሸት እንደሆኑ እርግጠኛ ሆነን በምናውቃቸው ነገሮች እየዋሹ ወነጀሉት፡፡ ታማኝ የሆኑ ዑለማዎች ግን መስክረውለታል፡፡ ለምሳሌ ገራገሩ ሸይኽ ዐብዱልዐዚዝ ኢብኑ ባዝ በህዝብ ፊት በታላቁ የሪያድ መስጂድ አድንቀውታል፡፡ ሌሎችም ሰውየውን ጠንቅቀው የሚያውቁት ዓሊሞች አድንቀውታል፡፡ አላህ ሰፊ የሆነ እዝነትን ይዘንለት፡፡ ለኢስላምና ለሙስሊሞች ባበረከተው መልካም ስራም ይሸልመው፡፡”
በፅሁፌ ላይ የተጠቀምኳቸውን መረጃዎች ከፊሉን በዚህ ሊንክ ገብተው ማግኘት ይችላሉ፡ 1. http://www.ajurry.com/vb/showthread.php?t=21064
ከሸይኽ ሙሐመድ አማን አልጃሚ ጋር በተያያዘ የቢድዐ አንጃዎች የሚያራግቡት ወሬ አንዳች ጥርጣሬ ካጫረበዎት ይህን ድምፅ ያውርዱና ያድምጡ፡፡ እያንዳንዷን ውንጀላ እየመዘዘ ይመልሳል፡፡ (ዐረብኛ ነው) https://www.youtube.com/watch?v=l_aVx9I9H7k
ሼር በማድረግ ከዑለማዎቻችን እንከላከል፡፡