Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

“ሱናህ” ማለት ምን ማለት ነው?

“ሱናህ” ማለት ምን ማለት ነው?
“ሱናህ” ማለት ብዙሃኑ ህዝብ ዘንድ ያለው ፍቺው ቢሰሩት አጅር የሚያስገኝ ቢተውት ግን የማያስቀጣ የዒባዳ አይነት የሚል ነው፡፡ ይሄ ግን ዘግይቶ የመጣ ፊቅሃዊ ፍቺ ነው፡፡ በተለያዩ የነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ሐዲሦች ላይ የሚገኘውን “ሱናህ” የሚል ቃል በዚህ መልኩ ከፈታነው ስህተት ላይ እንወድቃለን፡፡ ለምሳሌ ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም “በርግጥም ከናንተ በፊት ያሉትን ሰዎች ፈለጎች ( ‪#‎ሱናዎች‬) ትከተላላችሁ” ሲሉ ሶሐቦች “አይሁድና ክርስቲያኖችን ነው (ትከተላላችሁ) የምትለን?” ሲሉ “ታዲያ ማንን ነው?!” አሉ፡፡ ልብ ይበሉ በዚህ ሐዲሥ ላይ ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም የአይሁድና የክርስቲያኖችን ጥፉ አካሄድ “ሱናህ” ሲሉ ጠርተውታል፡፡ ይሄ እንግዲህ የሱናህ ቋንቋዊ ፍቺ እንደሆነ ያሳየናል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የትኛውም አካሄድ ወይም ፈለግ ሱናህ ይባላል ማለት ነው በቋንቋ ደረጃ፡፡
የነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አጠቃላይ አስተምሮም “ሱናህ” ይባላል፡፡ ይህን ግልፅ ከሚያደርጉልን ማስረጃዎች አንዱን እንመልከት፡
ሶስት ሰዎች ከነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ሚስቶች ዘንድ አንዷጋ ይሄዱና ስለ እሳቸው ዒባዳህ ይጠይቃሉ፡፡ ሲነገራቸው ጊዜ ቀለል አድርገው አዩት፡፡ ከዚያ ግን “እኛንና እሳቸውን ምን አገናኘን? እሳቸው እኮ ያለፈውም የሚመጣውም ወንጀላቸውን ይቅር ተብሎላቸዋል” ይላሉ፡፡ ከዚያም አንዱ “እኔ ከዚህ በኋላ ሌሊቱን ሁልጊዜ እሰግዳለሁ (አልተኛም)” አለ፡፡ ሌላው “እኔ አመቱን ሙሉ እፆማለሁ አላፈጥርም” አለ፡፡ ሌላው “እኔ ሴቶችን አገላለሁ (አልቀርብም)፡፡ በጭራሽ አላገባም” አለ፡፡ ከዚያ ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ወደነሱ በመሄድ “እናንተ ናችሁ እንዲህ እንዲህ ያላችሁት? ወላሂ እኔ ከናንተ በላይ አላህን ፈሪ እና የምጠነቀቀው ነኝ፡፡ ይሁን እንጂ እኔ እፆማለሁ አፈጥራለሁ፡፡ (ሌሊቱንም) እሰግዳለሁ እተኛለሁ፡፡ ሴቶችንም አገባለሁ፡፡ ‪#‎ከሱናዬ_የዞረ_ከኔ_አይደለም‬!!” አሉ፡፡ (ቡኻሪና ሙስሊም)
ይስተዋል!! በዚህ ሐዲሥ ላይ “ሱናህ” ተብሎ የተገለፀው ትርፍ ዒባዳህ ለማለት አይደለም፡፡ ምክኒያቱም “ግዴታ ያልሆነን ዒባዳ የተወ ከኔ አይደለም” አይሉምና ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም፡፡ ይልቁንም እያሉ ያሉት ከኔ ፈለግ ያፈነገጠ ከኔ አይደለም ነው፡፡ ሸይኹል አልባኒ ረሒመሁላህ እንዲህ ይላሉ፡ “ሱናህ የሚለው ቃል በቋንቋ ደረጃ መንገድ ማለት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ መልእክተኛው ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም የነበሩበትን ቅን መመሪያና ብርሃን የሚያጠቃልል ነው- ግዴታም ይሁን ትርፍ ዒባዳህ፡፡ አሁን ያለው ሙያዊ ፍቺ ግን ግዴታ ያልሆነውን የነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ፍኖት ማለት ነው፡፡ ነገር ግን በአንዳንድ ሐዲሦች ላይ የመጣው ሱናህ የሚለው ቃል በዚህ ሙያዊ ፍቺ ሊተረጎም አይገባውም፡፡ ለምሳሌ መልእክተኛው ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም “ሱናየን አደራችሁን” ማለታቸው እና “ከሱናዬ የዞረ ከኔ አይደለም” ማለታቸው እንደምሳሌ መውሰድ ይቻላል፡፡” (ተሕዚሩ አስሳጂድ፡ 44)
ይህንን ግንዛቤ ከሚያጠናክሩልን የዑለማእ ንግግሮች ውስጥ አንድ ሁለቱን ብቻ ልጥቀስ፡
1. “ ‪#‎ሱናህ‬ ማለት የኑሕ መርከብ ነች፡፡ የተሳፈረባት ይተርፋል፡፡ ከሷ ወደ ኋላ የቀረ ግን ይሰምጣል፡፡” አልኢማም ማሊክ ረሒመሁላህ፡፡ ያስተውሉ!! አልኢማም ማሊክ በዚህ ንግግራቸው ላይ እያነሱ ያለው ስለ ትርፍ ዒባዳህ ሳይሆን አጠቃላይ ስለነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አስተምሮ ነው፡፡ በሚገባ ያጢኑት፡፡
2. “ኢስላም ማለት #ሱናህ እንደሆነ እና ሱና ማለትም ኢስላም እንደሆነ እወቁ፡፡ አንዱ ያለ ሌላው ፀንቶ አይቆምም፡፡” አልኢማም አልበርበሃሪ ረሒመሁላህ፡፡ ረጋ ብለው ይመልከቱት፡፡
3. “ቢድዐህ ከልዩነት ጋር የተቆራኘች ናት፡፡ ልክ #ሱናህ ከመሰባሰብ ጋር የተቆራኘች እንደሆነችው፡፡ የ #ሱናህ እና የጀማዐህ ሰዎች ይባላል፡፡ ልክ የቢድዐህ እና የልዩነት ሰዎች እንደሚባለው፡፡” ኢብኑ ተይሚያህ ረሒመሁላህ፡፡
በነዚህ የዑለማእ ንግግሮች ውስጥ “ሱናህ” የሚለው ቃል በጥቅሉ የነብዩን ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አካሄድ እንጂ ትርፍ ዒባዳህ ማለት እንዳልሆነ እጅግ ሲበዛ ግልፅ ነው፡፡ ህዝባችን ዘንድ በሰፊው የሚታወቀው የሱናህ ፍቺ ግን ትርፍ ዒባዳህ ማለት እንደሆነ አሳልፈናል፡፡ ከዚህ ፍቺ በትይዩ ያለው ግዴታ ዒባዳህ ነው፡፡
የነብዩን ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አካሄድና መንገድ “ሱናህ” ብለን ስንጠራ ግን ከቢድዐ ትይዩ ያለውን ነው፡፡ ሰዎች ግን በሰፊው የሚያውቁት ዘግይቶ የመጣውን ፊቅሃዊ ፍቺውን ስለሆነ በዚህ ላይ ግንዛቤ የመሙላት ስራ ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ ያለበለዚያ ለነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ሐዲሦች እና ለቀደምት ዑለማዎች ንግግሮች የተዛባ ፍቺ እንድንሰጥ ያደርገናል፡፡ ይሄ ደግሞ አደገኛ ነገር ነው፡፡ በጥቅሉ “ሱናህ” ማለት የተፈጠርንበትን አላማ ማለትም አምልኮትን እንዴት መፈፀም እንዳለብን የሚያሳይ ነብያዊ የአፈፃፀም መመሪያ ወይም “ማኑዋል” ነው ማለት ነው፡፡ በዚህ አተናተንም “ሱናህ” ማለት ትርፉንም ግዴታውንም ዒባዳ የሚያጠቃልል ነው፡፡ እንዳውም ከግዴታ ዒባዳዎችም ባለፈ መሰረታዊ የዐቂዳህ ርእሰ-ጉዳዮችን ሁሉ የሚያቅፍ ነው- “ሱናህ”፡፡ ለዚህም ነው ታላላቅ ቀደምቶች ትክክለኛውን የነብዩን ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አስተምሮ ግልፅ ያደረጉባቸውን እና ጠማማ አስተሳሰቦችን ያጋለጡባቸውን ኪታቦቻቸውን “አስሱናህ” እያሉ መጥራታቸው፡፡ ለምሳሌ፡-
1. “አስሱናህ” የዐብዱላህ ኢብኒ አልኢማም አሕመድ ኪታብ
2. “አስሱናህ” የአልኢማም አልበገዊ ኪታብ
3. “ሸርሑ አስሱናህ” የአልኢማም አልበርበሃሪ ኪታብ
4. “ኡሱሉ አስሱናህ” የአልኢማም አሕመድ እና ሌሎችም
ከዚህ በመነሳት ያልተበከለውን የነብዩን ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አስተምህሮት የሚከተለውን ሰው “ሱኒ” ስንለው አጠቃላይ ስብስቡን ደግሞ “አህሉስሱናህ” እንላለን፡፡ ይሄ ስያሜ ከጥንት ሰለፎች ዘንድ ጀምሮ የሚታወቅ እንጂ መጤ ነገር አይደለም፡፡
ወላሁ አዕለም