Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ሰዎች መቼ ተለያዩ ?

Sadat Kemal Abu Nuh 
June 6 

ከፅሁፉ መሃል የተወሰደ
ኢማሙ ማሊክ እንዲህ ይላሉ ‹‹የዚህ ህዝብ መጨረሻው የሚስተካከለው፤ የመጀመሪያውን (ህዝብ) በተስተካከለበት መንገድ ብቻ ነው››፡፡ እሱም ነብዩ (ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም) ቅድሚያ ለተውሂድ በመስጠታቸው ነው፡፡
ሰዎቹ ሁሉ አንድ ሕዝብ ነበሩ፤ (ተለያዩ)
የአላህ የእምነት ገመድ ለሽርክ ቦታ የላትም፡፡1) አንድነት በምን ይፈርሳል???2) አላህ መቼ ነው መልክተኛን የሚልከው ???3) ሙስሊሞች ምንን ሲያጓድሉ ነው፤ ሰላም እና ደህንነት የሚያጡት???
በአላህ ፍቃድ የዛሬው ትምህርት የሚያጠነጥነው 
1) አንድነት በምን ይፈርሳል???ታላቁ ሰሃባ አብደላህ ኢብን መስኡድ (ረድየላሁ አንሁም) ኢማሙ ቡኻሪ በሰሂሃቸው በዘገቡላቸው እንዲህ ይላሉ ‹‹በአደም (አለይሂ ሰላም) እና ኑህ (አለይሂ ሰላም) መካከል 10 ቀርን ነበር፡፡ ሁሉም በኢስላም ላይ ነበሩ››፡፡ 
የሰው ልጆችን አንድ የሚያደርጋቸው፤ አላህ እነሱን የፈጠረበት ተውሂድ (እሱን በብቸኝነት ማምለክ) መተግበራቸው ነው፡፡ የሰው ልጆች ከብቸኛው አጋር ከሌለው ፈጣሪ ውጭ ያለን ፍጡር ሲያመልኩ አላህ መልክተኞችን በየዘመኑ ይልካል፤ አብሳሪና አስጠንቃቂ ሲሆኑ፡፡ እውነተኛው የአማኞች አንድነት እንደተጠበቀ እንዲቀጥል፤ አጋሪያን ይገሰፁ እና ይመለሱ ዘንድ መልክተኞችን ይልካል፡፡ ልዩነት የሚያመጣው አስል (ዋና መሰረት) የሆነውን የአላህ ተመላኪነት ትቶ ፍጡራን በማምለክ ሽርክ ውስጥ ሲገባ ነው፡፡ ለዚህ ሁሉ ማስረጃው የሚከተለው የአላህ ቃል ነው፡፡
كَانَ ٱلنَّاسُ أُمَّةً وَٰحِدَةً فَبَعَثَ ٱللَّهُ ٱلنَّبِيِّۦنَ مُبَشِّرِينَ وَمُنذِرِينَ وَأَنزَلَ مَعَهُمُ ٱلْكِتَٰبَ بِٱلْحَقِّ لِيَحْكُمَ بَيْنَ ٱلنَّاسِ فِيمَا ٱخْتَلَفُوا۟ فِيهِ ٍ
ሰዎቹ ሁሉ አንድ ሕዝብ ነበሩ፤ (ሽርክ በመከሰቱ ምክንያት አማኞች ከከሃዲያን ተለያዩ)፡፡ አላህም ነቢያትን አብሳሪዎችና አስፈራሪዎች አድርጎ ላከ፡፡ ከእነርሱም ጋር መጻሕፍትን (ተውሂዱን ከሽርክ፤ ሃቁን ከባጢል የሚለይ የሆነ) በሰዎቹ መካከል በዚያ በርሱ በተለያዩበት ነገር ይፈርድ ዘንድ በእውነት አወረደ፡፡ 
كَانَ ٱلنَّاسُ أُمَّةً وَٰحِدَةً ሰዎቹ ሁሉ አንድ ሕዝብ ነበሩ (ተለያዩ)፡፡ 
ብሎ የጠራቸው በተውሂድ ላይ አንድ ስለ ነበሩ ነው፡፡ ሽርክ ሲሰሩ በእርግጥ ተለያዩ፡፡ልክ ተውሂድን ትተው የሚከተሉትን 5 ደጋግነታቸው በአብደላህ ኢብን አባስ (ረድየላሁ አንሁም) አንደበት የተመሰከረላቸውን፤ በዛ ዘመን የነበሩት ኑህ የተላኩባቸው ህዝቦች እነዚህን 5 ደጋግ ሰዎች ሲያመልኩ እና የአላህን መብት አሳልፈው ሲሰጡ ተለያዩ፡፡ አላህም ሃቅን ከባጢል ይለይ ዘንድ መልክተኛውን ኑህ አለይሂ ሰላም ላከ፡፡ አብሳሪ እና አስጠንቃቂ ሲሆን ነብየላህ ኑህ፡፡
وَقَالُوا۟ لَا تَذَرُنَّ ءَالِهَتَكُمْ وَلَا تَذَرُنَّ وَدًّا وَلَا سُوَاعًا وَلَا يَغُوثَ وَيَعُوقَ وَنَسْرًاአሉም «አምላኮቻችሁን አትተዉ፡፡ ወድንም፣ ሱዋዕንም፣ የጉሥንም፣ የዑቅንም ነስርንም አትተው፡፡ 
ከአላህ ውጭ 5ቱ ደጋግ ሰዎች ሲመለኩ የሙስሊሞች አላህ ‹‹አንድ ህዝብ›› ብሎ ጠርቷቸው የነበሩት፤ ተከፋፍለው ሃቅ እና ባጢል ተለየ፡፡ ያመኑት አላህ እንዲህ ሲል የጠቀሳቸው <<ከሱ (ከኑህ) ጋር ጥቂቶች እንጂ አላመኑም>> ጥቂት ሲሆኑ፤ አመፀኞቹ ደግሞ መንገድ ስተው ብዙ ነበሩ፡፡ ግን የአላህ ቅጣት ሲመጣ ምንም አልበጃቸውም፤ በቁጥር በምዛታቸው፤ ጥፋትን እንጂ ሌላ አልጨመረላቸውም፡፡
ዛሬ ልክ እንደ ድሮው የኑህ ህዝቦች አለም ላይ ግማሹ ‹‹አልይ፤ ሁሴን፤ ፋጢማ፤ ዘይነብ፤ ሀሰን›› እያለ ሲጠራ (ልብ ሊባል የሚገባው እነዚህ ደጋግ መሆናቸው በአላህ መላክተኛ (ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም) አንደበት የተመሰከረላቸው ሲሆኑ) ሌሎች ደግሞ ሰዎች ዘንድ ደጋግ ተብለው ቢወሰዱም አላህ ዘንድ ገና ፍርዳቸው ያልታወቀ፤ ሰዎች የአላህን መብት አሳልፈው ይሰጧቸዋል፤ ለምሳሌ አብድልቃድር ጀይላኔ፤ አህመድ በደዊ፤ ባባ ፈሪዱ ዲን፤ ኑር ሁሴን፤ ቃጥባሬ፤ አብሬት፤ አባድር፤ አሊ ጎንደር፤ ደግዬ እና የመሳሰሉት፡፡ 
የአላህን መብት በኑህ (አለይሂ ሰላም) ዘመን ለነበሩት 5 ደጋግነታቸው በአብደላህ ኢብን አባስ (ረድየላሁ አንሁም) የተመሰከረላቸው አሳልፎ መስጠት ሽርክ ከሆነ እና አንድነት ከእንደዚህ አይነት አካላት ጋር ካልተቻለ፤ እነሱን ከማስተማር ውጪ፤ ታድያ ዛሬ በዘመናችን ገና አላህ ዘንድ ፍርድ ያልተሠጠባቸውን ሰዎች የሚያመልኩ ሰዎችን ሽርክ ላይ መሆናቸውን አለመንገር፤ ብሎም አልፎ እነሱን ‹‹አንድ ነን›› ብሎ መጥራቱ ምን ይሉታል???
2) አላህ መቼ ነው መልክተኛን የሚልከው ???አላህ መልክተኛን የሚልከው ህዝቦች ከአላህ ውጭ ያለን ሲያመልኩ፡፡ መልክተኞችን አስፈራሪ እና አብሳሪ አድርጎ ይልካቸዋል፡፡ 
3) ሙስሊሞች ምንን ሲያጓድሉ ነው፤ ሰላም እና ደህንነት የሚያጡት???የሚቀጥለውን አለም ምንም ጥርጥር የለውም የሚወርሷት የእምነት ባለቤቶች ብቻ ናቸው፡፡ ምድራዊው አለም ላይስ ደስታ እና የተመቻቸ ህይወት፤ ስቃይ መከራ የሌለበት የተድላ ህይወት በምን ይገኝ?
አላህ እንዲህ ይላል
مَنْ عَمِلَ صَٰلِحًا مِّن ذَكَرٍ أَوْ أُنثَىٰ وَهُوَ مُؤْمِنٌ فَلَنُحْيِيَنَّهُۥ حَيَوٰةً طَيِّبَةً ۖ وَلَنَجْزِيَنَّهُمْ أَجْرَهُم بِأَحْسَنِ مَا كَانُوا۟ يَعْمَلُونَ <<ከወንድ ወይም ከሴት እርሱ አማኝ ኾኖ በጎን የሰራ መልካም ኑሮን በእርግጥ እናኖረዋለን፡፡ ይሠሩትም ከነበሩት ነገር በመልካሙ ምንዳቸውን እንመነዳቸዋለን፡፡ >>
የአላህ ቃል በግልፅ እንዳስቀመጠው፤ መልካም ኑሮ ለማግኘት አምኖ መልካም ስራ መስራት ብቻ ነው፡፡ መልካም ስራ ይሆን ዘንድ ማንኛውም ስራ ለአላህ ብቻ ተብሎ ሊሰራ እና የነብያችንን(ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም) ፈለግ መከተል ግድ ይለዋል፡፡ ሀይማኖቱ እንዲመቻችለት፤ ሰላምን ማግኘት የፈለገ፤ የምድር ምትክ መሆን የፈለገ፤ በጠላት ላይ የበላይ ሆኖ ተከብሮ መኖር የፈለገ ምን ማድረግ እንዳለበት አላህ ሲናገር እንዲህ ይላል፡፡
وَعَدَ ٱللَّهُ ٱلَّذِينَ ءَامَنُوا۟ مِنكُمْ وَعَمِلُوا۟ ٱلصَّٰلِحَٰتِ لَيَسْتَخْلِفَنَّهُمْ فِى ٱلْأَرْضِ كَمَا ٱسْتَخْلَفَ ٱلَّذِينَ مِن قَبْلِهِمْ وَلَيُمَكِّنَنَّ لَهُمْ دِينَهُمُ ٱلَّذِى ٱرْتَضَىٰ لَهُمْ وَلَيُبَدِّلَنَّهُم مِّنۢ بَعْدِ خَوْفِهِمْ أَمْنًا ۚ يَعْبُدُونَنِى لَا يُشْرِكُونَ بِى شَيْـًٔا ۚ وَمَن كَفَرَ بَعْدَ ذَٰلِكَ فَأُو۟لَٰٓئِكَ هُمُ ٱلْفَٰسِقُونَ 
‹‹አላህ እነዚያን ከእናንተ ያመኑትንና መልካም ሥራዎችን የሠሩትን እነዚያን ከእነሱ በፊት የነበሩትን እንደተካ በምድር ለይ በእርግጥ ሊተካቸው፣ ለእነሱም ያንን የወደደላቸውን ሃይማኖታቸውን ሊያደላድልላቸው፣ ከፍርሃታቸውም በኋላ ጸጥታን ሊለውጥላቸው ተስፋን ቃል ሰጥቷቸዋል፡፡ በእኔ ምንንም የማያጋሩ ኾነው ይግገዙኛል፡፡ ከዚያም በኋላ የካደ ሰው እነዚያ እነርሱ አመጸኞች ናቸው፡፡›› 
አላህ በሰጠን ንፁህ አእምሮ ስናየው አንቀፁ በግልፅ እንዳስቀመጠው፤ ከላይ የጠቀስናቸውን ሁሉ ለማግኘት፤ አላህ እንደመስፈርት ያስቀመጠው ‹‹በእኔ ምንንም የማያጋሩ ኾነው ያምልኩኝ ይገዙኝ›› ይላል አላህ፡፡
ይሄ ከፀሃይ በላይ ግልፅ የሆነ አንቀፅ እስቲ የአገራችንን ተጨባጭ ሁኔታ እንድንፈትሽ ያድርገን፡፡ ኢትዬጵያ ውስጥ ስንት ቀብሮች ይመለካሉ፤ መንዙማ በሚል ስም ከአላህ ውጭ ስንቶች የአላህ መብት ይሰጣቸዋል፤ ከአላህ ውጭ ያለ ይመለካል፤ ይህ ሁሉ እያለ አላህ ካዘነላቸው ጥቂቶች ውጭ ወደ አላህ መንገድ እንጣራለን የሚሉም የነብያትን ፈለግ ተከትለው ተውሂድን ማስተማር ሲገባቸው፤ አይደለም በተውሂድ ሊጀምሩ፤ የዳእዋቸው መጨረሻም አላደረጉትም፡፡ በጣም የሚገርመው ግን ይህ ሁሉ ሽርክ እያለ ‹‹አንድ ነን›› የሚባለው ከባድ የሆነ ሰዎችን ባሉበት ጥመት ላይ የመተው ጭካኔ ከባዱ በደል ነው፡፡
አንዳንዶች እንዚህን ሁሉ ሽርኮች ጠንቅቀው እያዩ እና እያወቁ ተውሂድ እና ሱና ካልተስተካከሉ ምንም ፍሬ የማያፈሩ አርስቶችን ሰዉን ይሰብኩታል፡፡ ተውሂድ እና ሱና ካልተስተካከለ ምንም አይነት ስራ በአላህ መንገድ ላይ መታገልም ይሁን፤ ፆምም ይሁን፤ ስግደትም ይሁን፤ ምፅዋትም ይሁን፤ ሃጅም ይሁን ሌላም ሌላም ዋጋ የላቸውም፡፡
ሁለቱ የስራ መስፈርቶች ለአላህ ብሎ መስራት እና የነብዩን (ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም) ሱና ገጥሞ መገኘት ነው፡፡ አላህን በብቸኝነት ሳያመልኩ፤ የነብዩን (ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም) ፈለግ ሳይከተሉ የሰሩት ስራ ውድቅ ነው፡፡ ስራም አይባልም፡፡ ሽርክም እያለ ፤የሃይማኖት መመቻቸት፤ በሰላም ከፍርሃት ተጠብቆ መኖር፤ የምድር ምትክ መሆን፤ በጠላት ተከብሮ እና ተፈርቶ መኖር ፈፅሞ አይታሰብም፡፡
ሰዎች እንዴት ያስባሉ የአላህን መብት ሳያሟሉ ፍጡራን ለነሱ ፍትሃዊ እንዲሆኑላቸው፡፡ አላህን የፈራ ሁሉም ይፈራዋል፡፡ አላህን ያመፀ፤ ሁሉንም ይፈራል፡፡ 
ገርሞ የሚገርመው ደግሞ አንድነት በታታኝ ስለሆነው ስለ ሽርክ እና ቢድአ አስከፊነት ትምህርት ሲሰጥ ፌስቡክ እና ሌሎች ሚድያዎች ላይ ‹‹አትከፋፍሉን፤ አንድ ነን›› የሚባለው ከኢስላም አስተምህሮት ጋር በፍፁም የማይሄደው የተሳሳተ አካሄድ ነው፡፡ አላህ አንድ ሁኑ ሲል በእምነት ገመድ እንጂ ሽርክ እና ቢድዐን ይዛችሁ አላለም፡፡ ወይ ከምንም ነገር በፊት ነብያት እንዳስቀደሙት ተውሂድን አስቀድሞ ለህዝባችን ማድረስ፤ አለበለዚያ ይህንን ማድረግ ያልቻለ፤ ሰዎች ሲያስተምሩ እንቅፋት አለመሆን፤ እና ለነሱም መጥፎ ስም አለመለጠፍ፡፡ 
ኢማሙ ማሊክ እንዲህ ይላሉ ‹‹የዚህ ህዝብ መጨረሻው የሚስተካከለው፤ የመጀመሪያውን (ህዝብ) በተስተካከለበት መንገድ ብቻ ነው››፡፡ እሱም ነብዩ (ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም) ቅድሚያ ለተውሂድ በመስጠታቸው ነው፡፡
አላህ እውነተኛ አንድነት ይስጠን፡፡ እሱ እንዳለው በተውሂድ ላይ ተሳስረን አንድ የምንሆን ያድርገን፡፡ የአላህ የእምነት ገመድ ለሽርክ ቦታ የላትም፡፡
አላህ ሆይ! ሃቅን በሃቅነቱ አሳየን የምንቀበለውም አድርገን፤ ባጢልን በባጢልነቱ አሳየን የምንርቀውም አድርገን፡፡የአላህ ሰላት እና ሰላም በነብያት ሁሉ መደምደሚያ በአበል ቃሲም ላይ ይሁን፡፡