Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

እውን ኢብኑ ተይሚያ መውሊድን ፈቅደዋል?




እውን ኢብኑ ተይሚያ መውሊድን ፈቅደዋል?
~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~
ብዙ ሱፍዮች ኢብኑ ተይሚያን የመውሊድ ደጋፊ አስመስለው ሲያቀርቡ ያጋጥማሉ። ይሄ ግን የለየለት ማጭበርበር ነው። ሸይኹ እንዲህ ብለዋል፡-
الأعياد شريعة من الشرائع، فيجب فيها الاتباع، لا الابتداع. وللنبي صلى الله عليه وسلم خطب وعهود ووقائع في أيام متعددة: مثل يوم بدر، وحنين، والخندق، وفتح مكة، ووقت هجرته، ودخوله المدينة، وخطب له متعددة يذكر فيها قواعد الدين. ثم لم يوجب ذلك أن يتخذ أمثال تلك الأيام أعيادًا. وإنما يفعل مثل هذا النصارى الذين يتخذون أمثال أيام حوادث عيسى عليه السلام أعيادًا، أو اليهود، وإنما العيد شريعة، فما شرعه الله اتبع. وإلا لم يحدث في الدين ما ليس منه.
“በዓላት ከሃይማኖታዊ ድንጋጌዎች ውስጥ አንድ ድንጋጌ ናቸው። ስለሆነም በነሱ ላይ አዲስ መፍጠር ሳይሆን መረጃን መከተል የግድ ይላል። ለነብዩ ﷺ በተለያዩ ቀናት የተፈፀሙ ኹጥባዎች፣ ቃል-ኪዳኖችና ጦርነቶች አሏቸው። ለምሳሌ የበድር ጦርነት፣ የሑነይን፣ የምሽጉ (ኸንደቅ) ጦርነት፣ የመካ መከፈት፣ የስደታቸው ጊዜ፣ መዲና መግባታቸው፣ የዲን መሰረቶችን ያወሱባቸው በርካታ ድስኩሮች አሏቸው። ይሁን እንጂ ይሄ እንዲህ አይነት ቀናትን በዓላት አድርገው እንዲይዙ አላስገደደም። እንዲህ አይነቱን የሚሰሩት ክርስቲያኖች ናቸው። የዒሳ የተለያዩ ክስተቶች የተፈፀሙባቸውን ቀናት በዓላት አድርገው የሚይዙ የሆኑት። ወይም ደግሞ የሁዶች ናቸው (እንዲህ አይነቱን የሚሰሩት።) ዒድ ሸሪዐ ነው። አላህ የደነገገው ሊከተሉት ይገባል። ያለበለዚያ ግን ከዲን ያልሆነ ነገር በዲን ውስጥ አይፈጠርም።”
ለተንኮል የሚጠቀሙት የሸይኹ ንግግር እንዲህ የሚል ነው፡-
فتعظيم المولد، واتخاذه موسمًا، قد يفعله بعض الناس، ويكون له فيه أجر عظيم لحسن قصده، وتعظيمه لرسول الله صلى الله عليه وسلم، كما قدمته لك أنه يحسن من بعض الناس، ما يستقبح من المؤمن المسدد.
“የነብዩን ﷺ መውሊድ ማላቅና ህዝባዊ በዓል አድርጎ መያዝ አንዳንድ ሰው በጥሩ ኒያና የአላህ መልእክተኛን ﷺ በማላቁ ሲሰራው ምንዳ ሊኖረው ይችላል። እንዳሳለፍኩልህ የተቃና አማኝ ቢያደርገው የሚያስፀይፍ የሆነ ነገር አንዳዱ ሰው ጋር ግን እንደ በጎ ይቆጠራል።”
ንግግራቸውን በጥሞና ላስተዋለ መውሊድ ከሳቸው ዘንድ ፀያፍ እንደሆነ በቀላሉ ይደርስበታል፡፡ ምንዳ እንደሚያገኝ የተናገሩት የድርጊቱን ጥፋትነት ለማያውቅ ነው፡፡ ያውም በጥሩ ኒያውና በውስጡ ባሉ ሸሪዐዊ ተግባራት እንጂ በቢድዐው አጅር ያገኛል አላሉም። ይሄው ንግግራቸው፡-
وكذلك ما يحدثه بعض الناس، إما مضاهاة للنصارى في ميلاد عيسى عليه السلام، وإما محبة للنبي صلى الله عليه وسلم، وتعظيمًا. والله قد يثيبهم على هذه المحبة والاجتهاد، لا على البدع- من اتخاذ مولد النبي صلى الله عليه وسلم عيدًا.
“ልክ እንደዚሁ በዒሳ ﷺ ልደት ከክርስቲያኖች ጋር ለመፎካከር ሲል ወይም ደግሞ ነብዩን ﷺ ለመውደድና ለማክበር ሲሉ አንዳንዶች የሚፈጥሩትም ከዚሁ ነው። አላህ በዚህ (ለሳቸው) ባላቸው ውዴታና ጥረት ሊመነዳቸው ይችላል። የነብዩን ﷺ ልደት በዓል አድርገው በያዙበት በቢድዐው ግን አይደለም!”
ይህን እያየም “ኢብኑ ተይሚያ በመውሊድ አጅር ይገኛል ብለዋል” የሚል ሰው ዋሾ ነው፡፡ አያይዘውም እንዲህ ብለዋል፡-
“ሰዎች በልደት ቀናቸው ላይ ከመወዛገባቸው ጋር ማለት ነው።በጎ ቢሆን እንዲሰራ የሚያደርገው ሁኔታ ከመኖሩና ከልካይ ነገር ካለመኖሩም ጋር ሰለፎች ግን ይህንን አልሰሩትም። ይሄ ሙሉ ለሙሉ ወይም ሚዛን በሚደፋ መልኩ በጎ ቢሆን ኖሮ ሰለፎች ረዲየላሁ ዐንሁም ከኛ ይልቅ ለሱ የተገቡ ነበሩ። ምክንያቱም ለአላህ መልእክተኛ ﷺ ከኛ የበለጠ ወዳጆችና አክባሪዎች ነበሩና። እነሱ በመልካም ነገር ላይ ይበልጥ የጓጉ ነበሩ። በተሟላ መልኩ እሳቸውን መውደድና ማላቅ የሚገኘው እሳቸውን በመከታተል፣ በመታዘዝና ነገራቸውን በመከተል፣ በስውርም በግልፅም ፈለጋቸውን ሕያው በማድረግ፣ የተላኩበትን በማሰራጨትና በልብም በእጅም በምላስም በዚህ ላይ በመታገል ነው። ይህቺ ናት ከሙሃጂሮችና ከአንሷሮች የሆኑት እነሱንም በመልካም የተከተሉት የመጀመሪያዎቹ ቀዳሚዎች መንገድ። [ኢቅቲዳ አስሲራጦል ሙስተቂም፡ 2/115-116፣ 123-126]
በነገራችን ላይ መሰረቱ ቢድዐ የሆነ ተግባር በውስጡ አንዳንድ መልካም ስራዎች ስለኖሩበት በመልካም ኒያ አጅር እንደማይገኝበት ዑለማዎች እርምት ይሰጣሉ። ነብዩ ﷺ “ቢድዐ ሁሉ ጥመት ነው” ማለታቸው ይታወስ፡፡ [ሙስሊም] ሶሐባው ኢብኑ ዑመርም “ቢድዐ ሁሉ ጥመት ነው፣ ሰዎች መልካም ነው ብለው ቢያስቡትም” ብለዋል፡፡ [ዳሪሚ ዘግበውታል፡፡] ኢብኑ መስዑድም በሌሊት መስጂድ ውስጥ ተሰባስበው ጠጠር ሰብስበው ዚክር ሲሉ የነበሩ ሰዎችን “አፈፃፀማችሁ መሰረት ባይኖረውም በዚክሩ ግን አጅር ታገኛላችሁ” አላሏቸውም፡፡ ይልቁንም“ነፍሴ በእጁ በሆነችው እምላለሁ! ወይ እናንተ ከሙሐመድ ሃይማኖት ይበልጥ የተቀና መንገድ ላይ ናችሁ! ወይ ደግሞ የጥመት በር ከፋቾች ናችሁ!” ነው ያሏቸው፡፡ “ኧረ እኛ መልካምን እንጂ ሌላ አላሰብንም” ሲሉም “ስንት መልካምን እያሰበ ፈፅሞ የማያገኘው አለ?!” ነው ያሏቸው፡፡ [አስሶሒሐህ፡ 2005] ታላቁ ሰለፍ የሕያ ኢብኑ የሕያ “ሱና ባልሆነ ነገር ውስጥ ተስፋና ምንዳ የለም” ብለዋል። [አልኢዕቲሷም፡ 1/199] ስለዚህ ባለማወቅም ይሁን በኢጅቲሃድ ቢሰራም ከቅጣት ሊተርፍ ይችላል እንጂ በምንም መልኩ መሰረቱ ቢድዐ በሆነ አምልኮ የሚገኝ ሽልማት የለም። ከራሳቸው ከኢብኑ ተይሚያ ይህን ሀሳብ የሚያፀኑ ሃሳቦች ብዙ ናቸው።
አሁንም መውሊድን አስመልክተው ሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚያ ረሒመሁላህ እንዲህ ብለዋል፡-
“በዚህ ርእስ ስር መጥፎ ከሆኑ ነገሮች ውስጥ ሌሎቹ በዓላትና ቢድዐዊ የሆኑት ዓውደ-አመታት ናቸው” ካሉ በኋላ ዘለግ ያለ ማብራሪያ ሰጥተዋል። [አልኢቅቲዳእ፡ 2/81-82]
የኢብኑ ተይሚያ ንግግር እየቆራረጡና እየቀጣጠሉ የሚንጠላጠሉ አካላትን ይበልጥ ወሽመጣቸውን መቁረጥ አስፈላጊ ስለሆነ ሌላም የሸይኹን ንግግር ልጨምር። በያመቱ የነብዩ ﷺ መውሊድ ሌሊት ላይ ኺትማ ስለሚያደርግ ሰው “ይሄ የተወደደ ነው ወይስ አይደለም?” ተብለው ተጠይቀው እንዲህ ብለው ነበር የመለሱት፡-
وَأَمَّا اتِّخَاذُ مَوْسِمٍ غَيْرِ الْمَوَاسِمِ الشَّرْعِيَّةِ كَبَعْضِ لَيَالِي شَهْرِ رَبِيعٍ الْأَوَّلِ الَّتِي يُقَالُ: إنَّهَا لَيْلَةُ الْمَوْلِدِ أَوْ بَعْضِ لَيَالِيِ رَجبٍ أَوْ ثَامِنَ عَشَرَ ذِي الْحِجةِ أَوْ أَوَّلِ جمْعَةٍ مِنْ رَجبٍ أَوْ ثَامِنِ شَوَّالٍ الَّذِي يُسَمِّيهِ الْجهَّالُ عِيدَ الْأَبْرَارِ فَإِنَّهَا مِنْ الْبِدَعِ الَّتِي لَمْ يَسْتَحِبَّهَا السَّلَفُ وَلَمْ يَفْعَلُوهَا.
“ሸሪዐዊ ያልሆኑ ክብረ በዓላትን ክብረ-በዓል አድርጎ መያዝ ግን ‘የመውሊድ ሌሊት’ የሚባሉትን የተወሰኑ የረቢዐል አወል ሌሊቶችን ወይም የረጀብ ሌሊቶችን ወይም ደግሞ ዙልሒጃ አስራ ስምንትን ወይም ደግሞ የረጀብ የመጀመሪያ ጁሙዐን ወይም ደግሞ መሃይማን ‘የደጋጎች ዒድ’ እያሉ የሚጠሩትን ሸዋል ስምንትን የመሰሉ እነዚህ ሰለፎች እንደሚወደዱ ያልገለጿቸውና ያልተገበሯቸው ቢድዐዎች ውስጥ ናቸው።” [መጅሙዑል ፈታዋ፡ 25/298]
ከዚህስ በኋላ በኢብኑ ተይሚያ ስም የሚነግድ ይኖር ይሆን? ለነገሩ ምን ይታወቃል? መቼስ የስሜትን ፈረስ በማስረጃ ልጓም መግታት አይቻል ነገር። ሌላም እናክል፡-
“… የሆኑ ሰዎች ልክ እንደ መደበኛ ሱናዎች ቋሚ ልምድ አድርገው ሳይዙ በሆኑ ሌሊቶች ግዴታ ላልሆነ ሶላት ቢሰባሰቡ ይሄ አይጠላም። ነገር ግን ወቅት በዞረ ቁጥር አብሮ የሚዞር ልምድ አድርጎ መያዙ የተጠላ ነው። ሸሪዐን መቀየር እንዲሁም የተደነገገውን ካልተደነገገው ጋር ማመሳሰል አለውና። እንዲህ አይነቱ ቢፈቀድ ኖሮ በረፋድ ወቅት ወይም በዙህርና በዐስር መካከል ሌላ ሶላት እንዲፈፀም ወይም በሸዕባን ተራዊሕ እንዲኖር ወይም በሁለቱ የዒድ ሶላቶች ላይ አዛን እንዲኖር ወይም ደግሞ በበይተል መቅዲስ ካለው ቋጥኝ ዘንድ ሐጅ እንዲኖር መፍቀድ ነበር። ይሄ የአላህን ዲን መቀየርና መለወጥ ነው። በመውሊድ ሌሊትና በሌሎችም ላይ ልክ እንዲሁ ነው የሚባለው።” ከምን አይነት ጥፋቶች ጋር አብረው እንደቆጠሩት ተመልከቱ። ቀጠሉ፡-
“የተጠላ ቢድዐ ማለት በሸሪዐው እንደሚወደድ ያልተገለፀ ሲሆን እሱም አላህ ያልፈቀደበትን መደንገጉ ነው። የሆነን ነገር ከአላህ ድንጋጌ ሳይኖር ዲንና መቃረቢያ ያደረገ ሰው ጠማማ ሙብተዲዕ ነው። እሱን ነው ነብዩ ﷺ ‘ቢድዐ ሁሉ ጥመት ነው’ ሲሉ የገለፁት። ፈጠራ የድንጋጌ ተቃራኒ ነው። ድንጋጌ ማለት ግዴታ በሆነ ትእዛዝ ወይም ተወዳጅ መሆንን በሚያመልክት ትእዛዝ አላህና መልእክተኛው ያዘዙት ነው። ልክ ለተራዊሕ በአንድ ኢማም እንደመሰባሰብ፣ ቁርኣንን በአንድ መፅሐፍ መሰብሰብ፣ አፈንጋጮችንና ኸዋሪጆችን እንደመዋጋት ያለና ይህን የመሳሰለ በሳቸው ዘመን ያልተፈፀመ ነገር ቢሆን እንኳን። አላህና መልእክተኛው ያልደነገጉት እርሱ ፈጠራ ነው፣ ጥመት። ለምሳሌ ልክ የሶላት ወቅቶችን፣ የጁሙዐና የበዓላት ቀናትን ደንጋጊው እንደወሰነው በሱ ውስጥ ለዒባዳ በመሰባሰብ የሆነን ቦታ ወይም የሆነን ጊዜ ለይቶ እንደ መያዝ ማለት ነው።” [መጅሙዑል ፈታዋ፡ 23/133-134]
መጤ የሆኑ በዓላትን በጅምላ የሚኮንኑባቸው ሌሎች ንግግሮችም አሏቸው። [አልኢቅቲዷእ፡ 2/115] [አልሙስተድረክ ዐላመጅሙዒል ፈታዋ፡ 3/132]
·
ከ “መውሊድ፤ ታሪክ፣ ስህተት፣ እርምት” መፅሐፍ ተነካክቶ የተወሰደ

Post a Comment

0 Comments