Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

በዙልሒጃ አስሩ ቀናት ውስጥ ፀጉርንና ጥፍርን መቁረጥን የሚመለከቱ ብይኖች

በዙልሒጃ አስሩ ቀናት ውስጥ ፀጉርንና ጥፍርን መቁረጥን የሚመለከቱ ብይኖች
‪#‎ጥያቄ_1‬ ፡- በዙልሒጃህ የመጀመሪያ 10 ቀናት ውስጥ ፀጉርንና ጥፍርን መቆረጥን መተው ከሱና ነው? ከሆነስ ኡዱሒያ የሚያርደውን ሰው ቤተሰቦችም ይጨምራል?
መልስ፡- (የዙልሒጃ) 10 ቀናት ከገቡ አንዳችሁ ኡዱሒያህ ማረድ የሚያስብ ከሆነ ከፀጉሩም ከጥፍሩም ምንም ሊቆርጥ አይገባውም” ማለታቸው ከነብዩ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ተረጋግጧል፡፡ በሌላ ዘገባ “ከሰውነቱም እንዲሁ” ይላሉ፡፡ ይሄ ክልከላ ነው፡፡ ክልከላ ደግሞ ክልክልነትን የሚያነሳ ማስረጃ ካልመጣ በስተቀር መሰረቱ ሐራምነትን ነው የሚጠቁመው፡፡
ከዚህም በመነሳት ኡዱሒያህ ሊያርድ ያሰበ ሰው የዙልሒጃ ወር ከገባ እርዱን እስከሚፈፅም ድረስ ከፀጉሩም፣ ከሰውነቱም፣ ከጥፍሩም ምንም ሊቆርጥ አይፈቀድለትም፡፡ ሐዲሡ የሚመለከተው ኡዱሒያ የሚያወጣውን እንጂ የሚወጣላቸውን (ቤተሰቡን) አይደለም፡፡ ምክኒያቱም ቤተሰቡ የሚታረድላቸው እንጂ ኡዱሒያ አራጆች አይደሉም፡፡
‪#‎ጥያቄ_2‬ ፡- ሆን ብሎ (ጥፍሩን ወይም ፀጉሩን) የቆረጠ የኡዱሒያ እርዱ ያብቃቃዋል (አይበላሽበትም)?
መልስ፡- … ሆን ብሎ ከቆረጠ የአላህ መልእክተኛን ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ወንጅሏል፡፡ ኡዱሒያው ግን ያብቃቃዋል (ውድቅ አይሆንበትም፡፡) ምክኒያቱም ኡዱሒያውና ፀጉርን ወይም ጥፍርን ወይም አካልን መቁረጥ ግንኙነት የላቸውምና፡፡ (መጅሙዑ ፈታዋ ወረሳኢል አልዑሠይሚን፡ 25/145) “ኡዱሒያ ሊያርድ ወስኖ ሳለ ሆን ብሎ ከፀጉሩ ወይም ከጥፍሩ ወይም ከአካሉ የሆነን ነገር የቆረጠ ወደ አላሁ ተዐላ ተውበት ሊያደርግ ይገባዋል፡፡ ዳግመኛም እንዳይፈፅም፡፡ ወንጀሉን ማበሻ የሚፈፅመው ማካካሻ (ከፋራ) የለበትም፡፡ አንዳንድ ሰዎች እንደሚያስቡት ኡዱሒያውን እንዳይፈፅም አያግደውም፡፡ ረስቶ ወይም (ብይኑን) ባለማወቅ ከቆረጠ ወይም ፀጉሩ ሆን ብሎ ሳያደርገው ቢወድቅ ወንጀል የለበትም፡፡ እንዲቆርጥ የሚያስገድድ አጋጣሚ ከኖረ መቁረጥ ይችላል፡፡ ምንም ወንጀል የለበትም፡፡ ለምሳሌ ጥፍሩ ተሰብሮ ቢያስቸግረውና ቢቆርጠው ወይም ፀጉሩ ከዐይኑ ገብቶ ቢያስወግደው፣ ወይም ቁስል ለማከም አስፈልጎ ቢያሳጥረው ወዘተ ችግር የለውም፡፡ (ኢብኑ ዑሠይሚን፣ ሙኽተሶሩ አሕካሙልኡዱሒያ ወዝዘካህ፡ 1/18)
‪#‎ጥያቄ_3‬ ፡- በዙልሒጃ ወር ኡዱሒያን ሳያርዱ በፊት ፀጉርን መሞሸጥ ብይኑ ምንድን ነው?
መልስ፡- … አንዲት ኡዱሒያ ማረድን ያሰበች ሴት ፀጉሯን መሞሸጥ ከፈለገች ምን ችግር የለባትም (መሞሸጥ ትችላለች፡፡) ባይሆን ቀስ ብላ ታበጥር፡፡ አውቃ ካልሆነ ከፀጉሯ የሆኑ ክፍሎች ቢወድቁ ወንጀል የለባትም፡፡ ምክኒያቱም እንዲወድቅ አስባ ሳይሆን ለማሳመር ነውና ያበጠረችው፡፡ እናም (ፀጉሯ) መንጠባጠቡ ታስቦበት አይደለም የተከሰተው፡፡ (ኢብኑ ዑሠይሚን፣ ኑሩን ዐለድደርብ፡ 13/2)
‪#‎ጥያቄ_4‬ ፡- አንድ ሰው ኡዱሒያን የነየተው የዙልሒጃ አስር ቀናት ከገቡ በኋላ ከሆነና ፀጉሩን ቆርጦ ከሆነ ኡዱሒያው ያብቃቃዋል (ትክክል ነው)?
መልስ፡ ሰውየው አስሮቹ ቀናት ከጀመሩ በኋላ ከሆነ ኡዱሒያን ሊያርድ የወሰነው ቀድሞ ከፀጉሩም፣ ከጥፍሮቹም ቆርጦ ከሆነ ኡዱሒያን ቢያርድ ችግር የለበትም፡፡ ከጥፍሩም ከፀጉሩም በመቁረጡም ወንጀለኛ አይሆንም፡፡ ምክኒያቱም ሳይወስን በፊት ነውና፡፡ (መጅሙዑ ፈታዋ ወረሳኢል አልዑሠይሚን፡ 25/150)
‪#‎ጥያቄ_5‬ ፡- በዙልሒጃ አስሩ ቀናት ውስጥ ፀጉርን፣ ጥፍርንና አካልን ከመቁረጥ የሚከለከለው እስከመቼ ነው?
መልስ፡- ኡዱሒያውን እስከሚያርድ ድረስ፡፡ ሲያርድ ክልከላው ይወገዳል፡፡ (መጅሙዑ ፈታዋ ወረሳኢል አልዑሠይሚን፡ 25/152)
‪#‎ጥያቄ_6‬ ፡- በዙልሒጃ አስሩ ቀናት ውስጥ መቁረጥ የተከለከለበት “ጥበቡ ምን ይሆን” የሚል ካለ
የዚህ መልስ በሁለት መልኩ ነው እንላለን፡፡
የመጀመሪያው፡- ጥበቡ የነብዩ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም መከልከል ነው፡፡ ነብዩ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አንድን ነገር መከልከላቸውም ማዘዛቸውም ለሆነ ጥበብ እንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ ይሄ አማኝ ለሆነ ሁሉ በቂ ነው፡፡ ምክኒያቱም የላቀው ጌታ (በመካከላቸው እንዲፈርዱ ወደ አላህ እና ወደ መልእክተኛው ሲጠሩ የአማኞች መልስ መሆን የነበረበት “ሰምተናል ታዘናል” ሊሉ ነበር፡፡ እነዚህ ናቸው ስኬታማዎቹ) ይላልና፡፡ በሶሒሕ ሐዲሥም ዓኢሻን ረዲየላሁ ዐንሃ አንዲት ሴት “ለምንድን ነው የወር አበባ ላይ የቆየች ሴት ፆሟን ቀዷ እያወጣች ሶላቷን ቀዷ የማታወጣው” ስትል ጠየቀቻት፡፡ ዓኢሻም እንዲህ አለቻት “ይሄ በነብዩ ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ዘመን ያገኘን ነበር፡፡ ፆምን ቀዷ እንድናወጣ ስንታዘዝ ሶላትን ግን ቀዷ እንድናወጣ አንታዘዝም ነበር፡፡”
ይህኛው መልስ ቀዳዳ የሚዘጋ ነው፡፡ ሊቃወሙት የማይቻል ቆራጭ መልስም ነው፡፡ እሱም የሸሪዐዊ ብይኖችን ጥበብ በተመለከተ “አላህና መልእክተኛው አዘውታል” እያሉ መመለስ ነው፡፡
ሌላኛው መልክ ደግሞ፡- በነዚህ አስሩ ቀናት ውስጥ ፀጉርን፣ ወይም ጥፍርን ወይም አካልን መቁረጥ የተከለከለበት ጥበቡ ምናልባትም ሰዎች በየሚኖርበት ሀገር ሆነው ሐጅና ዑምራ ላይ ያሉ ሰዎች በነዚህ ቀናት ውስጥ የሚሰሩትን በከፊል ለመጋራት ነው፡፡ ምክኒያቱም ሐጅ እና ዑምራ ላይ ያሉ ሰዎች ፀጉርንና ጥፍርን ከመቁረጥ መራቅ ይጠበቅባቸዋልና፡፡ ወላሁ አዕለም፡፡” ((መጅሙዑ ፈታዋ ወረሳኢል አልዑሠይሚን፡ 25/139)
ዙልሒጃ በኢስላማዊው አቆጣጠር 12ኛው ወር ነው፡፡ ዛሬ ሰኞ ዙልቂዕዳህ 27/1435 ነው፡፡ ስለዚህ ከሁለት ወይም ከሶስት ቀናት በኋላ ዙልሒጃህ ይገባል፡፡ ኡዱሒያ ሊያርዱ ወስነው ከሆነ ከወዲሁ ይዘጋጁ፡፡ ኋላ እንዳይቸገሩ ከወዲሁ ፀጉረዎን፣ ጥፍረዎን መላ ይበሉ፡፡
“ሼር” ማድረግ እንዳይረሱ፡፡ ከአጅሩ ይቋደሱ፡፡ የተረሳ ሱና ያስታውሱ፡፡
(ኢብኑ ሙነወር፣ መስከረም 12/2007)

Post a Comment

0 Comments