Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

የኢኽዋን ምሽጎችን ማንኮታኮት (ተከታታይ፣ ክፍል አራት)

የኢኽዋን ምሽጎችን ማንኮታኮት
(ተከታታይ፣ ክፍል አራት)
ኢኽዋን የዲን ነጋዴዎች!
አሕባሾችን ህፃናትን ሰብስበው በኩፍር ሲያሰለጥኗቸው የሚያሳይ ቪዲዮ ሰሞኑን ተመልክተናል፡፡ የአላህ ከፍጡራን በላይ መሆን ከአንድ ሺህ በላይ በሆኑ ማስረጃዎች የፀና ሐቅ ቢሆንም አሕባሾች ግን ከቁርኣንና ከሱናም ከህሊናም ጭምር በማፈንገጥ “አላህ የትም የለም” እያሉ ያለ ምንም ሀፍረት ባደባባይ እያስተጋቡ ነው፡፡ ከአእምሮ መታወር አላህ ይጠብቀን፡፡ (አላህም ብርሃን ያላደረገለትን ሰው ለርሱ ምንም ብርሃን የለውም፡፡” [አንኑር፡ 40] የአላህ ከዐርሹ በላይ መሆን በቁርኣን በሐዲሥ እንደተገለፀ እራሳቸው አሕባሾቹም ያውቃሉ፡፡ ስለሚያውቁም ነው “የቁርኣንና የሐዲሥን ግልፅ ወይም ዟሂር መልእክት መያዝ ኩፍር ነው” የሚሉት፣ ሌሎችንም በዚህ የሚወነጅሉት፡፡ የሚደንቀው የራሳቸው መጥመም አልበቃ ብሎ ይህን ጥመታቸውን ያልተቀበለን በጅምላ ማክፈራቸው ነው፡፡ በዚህ ጥፋታቸው አሕባሾች የጥንቱን ጠማማ አንጃ የጀህሚያህ እምነት እየተከተሉ እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ የአሕባሽ ቅድመ-አያት የሆኑት የጥንቶቹ ጀህሚያዎች የሚያመልኩት ጌታ የጠፋባቸው ደንባራ ፍጡሮች ናቸው፡፡ በዚህ ላይ ሰለፎች ምን እንደሉ እንመልከት፡
1. ታላቁ የበስራ ዓሊም ሰዒድ ኢብኑ ዓሚር (208 ሂ.) ረሒመሁላህ እንዲህ ይላሉ፡- “የጀህሚያዎች ንግግር ከአይሁድና ከክርስቲያን የከፋ ነው፡፡ አይሁድ፣ ክርስቲያንና የሌሎችም ሃይማኖት ተከታዮች አሸናፊውና የላቀው አላህ ከዙፋኑ ላይ እንደሆነ ከሙስሊሞች ጋር ተስማምተዋል፡፡ ጀህሚያዎች ግን ‘ምንም ላይ አይደለም’ አሉ፡፡” [ሙኽተሶሩልዑሉው፡ 168]
2. ኢብኑልሙባረክ ረሒመሁላህ እንዲህ ይላሉ፡- “ሁሉም ህዝቦች የሚያመልኩትን ያውቃሉ- ጀህሚያዎች ሲቀሩ፡፡” [ኸልቁ አፍዓሊልዒባድ፡ 20]
3. ኢብኑ ቁተይባህ ረሒመሁላህ (276 ሂ.)፡- “ህዝቦች በሙሉ ዐረቡም ሌላውም በተፈጥሯቸው አላህ በሰማይ ነው” ይላሉ፡፡ [ተእዊሉ ሙኽተለፊልሐዲሥ፡ 327-328]
ይህን በዚህ ላይ እናቁመውና ኢኽዋኖች ሰሞኑን የተለቀቀውን የአሕባሾች ስልጠና ተከትሎ “ተውሒድ ተውሒድ የምትሉ ሰዎች የት አላችሁ?” እያሉ መጮህ ይዘዋል፡፡ እርግጥ ነው የአሕባሽን ጥመት ለመጋፈጥ የተባበረ ክንድ ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን በአሕባሽ ላይ የሚደረገውን ዘመቻ በማጠናከር ፋንታ የሆነ አነጋጋሪ ክስተት እየጠበቁ ወደ ተውሒድ የሚጣሩ ሰዎችን በነገር መውጋቱ የሚያስተዛዝብ ነገር ነው፡፡ በሚያሳዝን ሁኔታ ሶሪያ ውስጥ እልቂት ተፈፀመ ከተባለ “ቅድሚያ ለተውሒድ የምትሉ የት አላችሁ?” ይላሉ፡፡ ኢማራት ውስጥ የሂንዱ ቤተ-ጣኦት ሲገነባ “ቅድሚያ ለተውሒድ የምትሉ የት አላችሁ?” ይላሉ፡፡ ማእከላዊ አፍሪካ ውስጥ ሙስሊሞች ተጨፈጨፉ “ቅድሚያ ለተውሒድ የምትሉ ሰዎች የት አላችሁ?” ይላሉ፡፡ የሆኑ ጋጠ-ወጥ ከሃዲዎች በኢስላምና በነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ላይ አሾፉ “ተውሒድ ተውሒድ የምትሉ ሰዎች የት አላችሁ?” ይላሉ፡፡ በየአጋጣሚው ክስተት እየጠበቁ ለተውሒድ ደዕዋ ያረገዙትን ጥላቻ ይዘረግፋሉ፡፡ ጠብቋቸው ወደፊትም ይህን መሰሪ አካሄዳቸውን አያቆሙም፡፡ አላማቸው ከማስረጃ የተኳረፈ አካሄዳቸውን ህዝበ-ሙስሊሙ ከጊዜ ጊዜ እየነቃበት ስለሆነ ስሜት ቀስቃሽ ክስተቶችን ጠብቀው እድሜ ለማራዘም መውተርተር ነው፡፡ ይሄው አሁንም አሕባሾች ብልሹ ዐቂዳቸውን ለህፃናት የሚያቀርቡበት ቪዲዮ መሰራጨቱን ተከትሎ እንደ ልማዳቸው “ቅድሚያ ለተውሒድ የምትሉ ሰዎች የት አላችሁ?” እያሉ ነው፡፡ ክፉ በሽታ!! ለመሆኑ እነሱስ የትኛው ፕላኔት ላይ ነው ያሉት?!
አዎ አሕባሾች የአላህን ከዐርሹ በላይ መሆን እያስተባበሉ የሚሰጡት ስልጠና እጅጉን አደገኛ የዐቂዳ ብክለት ነው፡፡ ግን አሁን ኢኽዋኖች እየጮሁ ያሉት እውነት ጥፋቱ አሳስቧቸው የሙስሊሞች ዐቂዳ አስጨንቋቸው ከሆነ ምነው ታዲያ የራሳቸው የኢኽዋን ቁንጮዎች ተመሳሳይ ጥፋት ሲጋለጥ ይንዘረዘራሉ?!! ለምንስ ከአሕባሾቹ ጥፋቶች በራእ እንደሚያደርጉት ከራሳቸው ሰዎች ጥፋትስ በራእ አያደርጉም? ለምንስ የነ ሰይድ ቁጥብ ብልሹ ዐቂዳ ሲነገር ያንቀጠቅጣቸዋል? እስኪ ሌሎቹን በርካታ የዐቂዳ ብክለቶች እናቆያቸውና አሁን በአሕባሽ አስታከው በነገር የሚወጉበትን ርእስ እንመልከት፡፡
ኢኽዋኖች በሚሊኒየሙ ስምምነት ያደረጉት የአላህን ከዐርሹ በላይ መሆን ከሚያስተባብሉ ሱፍዮች ጋር አይደለምን?
ኢኽዋኖች ቻግኒ ላይ ስምምነት ያደረጉት የአላህን ከዐርሹ በላይ መሆን ከሚያስተባብሉ ሱፍዮች ጋር አይደለምን?
ከራሳቸው ከኢኽዋኖች ቁንጮዎችስ ልክ እንደ አሕባሾች የአላህን ከዐርሹ በላይ መሆን የሚያስተባብሉ የሉምን?
በሌሎችስ ጥፋቶች (በሺርኩ፣ በመውሊዱ፣ በሙዚቃው፣…) አሕባሾችን የሚጋራ ከውስጣቸው ብዙ የሉምን?
መንዙማ ባዩ ሙሐመድ አወል በመንዙማው ውስጥ ልክ አሕባሾች እንደሚሉት “አላሁ መውጁዱን ቢላ መካን) (አላህ ያለ ቦታ ነው ያለው) እያለ ያንጎራጉራል፡፡ በሺርክ የተሞሉ መንዙማዎቹን በተመለከተም ያፈጠጠ ያገጠጠ ስለሆነ ነጋሪ አያሻም፡፡ የኛ ለዐቂዳ ተቆርቋሪዎች! እውነት የሙስሊሙ ዐቂዳ ካሳሰባችሁ ሰልፍ በምትቀሰቅሱባቸው “ድምፃችን ይሰማ” እና መሰል ሚዲያዎች አለፍ ብሎም በአፍሪካ ቲቪ ከነዚህ አካላት አስጠንቅቁ እስኪ?
እውነት የዐቂዳ ጉዳይ ካሳሰባቸው ምነው ሁሉንም ጥፋቶች አይዋጉም?
1. ልክ እንደ አሕባሹ መስራች ዐብደላህ አልሀረሪ የኢኽዋን አንጃ መስራች የሆነው ሐሰን አልበናም ሱፊ ነው፡፡ ያኛው ሪፋዒ ይሄኛው ሐሷፊ ሻዚሊ፡፡ (ሙዘኪራቱድደዕዋ ወድዳዒያህ) የሚለው ኪታቡ ላይ እሱ እራሱ ስለራሱ የፃፈውን ተመልከቱ፡፡ “አይ ሱፊ ነኝ ሲል የፈለገው ሌላ ነው” ወይም ደግሞ “ኋላ ላይ ከሱፊነቱ ተመልሷል” እያሉ ጭፍን አድናቂዎቹ ስለሚሟገቱ በዚህ ላይ ሌላ ጊዜ አብረን እናያለን ኢን ሻአላህ፡፡
2. ልክ እንደ አሕባሹ መስራች ዐብደላህ አልሀረሪ የኢኽዋን አንጃ መስራች የሆነው ሐሰን አልበናም መውሊድን ያከብር ነበር፡፡ ኧረ እንዳውም ሐሰን አልበና ረቢዑል አወል አንድ ካለ ጀምሮ እስከ 12 ድረስ ነበር መውሊድን የሚያከብረው፡፡ [ሙዘኪራቱድደዕዋ ወድዳዒያህ፡ 58]
3. ልክ በርካታ አሽዐርዮች የኢኽዋኒ መስራች ሐሰን አልበናስ በአስማእ ወስሲፋት ላይ በተፍዊድ አያምንምን? ተፍዊድ ማለት በአላህ ሲፋዎች ላይ ከሰለፎች የመጡትን የማስረጃዎቹን ቀጥተኛ ፍቺ “ማመሳሰል ይሰጣል” በሚል ሙግት ትርጉም ሳይሰጡ ማሳለፍ ሲሆን እነዚህ የተፍዊድ አራማጆች የሲፋዎቹን ቀጥተኛ መልእክት ባለመቀበል በኩል ከሌሎች የቢድዐህ አንጃዎች ጋር ተመሳሳይ አቋም አላቸው፡፡ እነዚህን ሰዎች አስመልክተው ኢብኑ ተይሚያህ ረሒመሁላህ እንዲህ ብለዋል፡“ሱናንና ሰለፎችን ተከታዮች ነን እያሉ የሚሞግቱት የተፍዊድ ሰዎች ንግግር አደገኛ ከሆኑት የሙብተዲዖችና የጥመት ሰዎች ንግግር ነው” ይላሉ፡፡ [ደርእ፡ 1/115]
4. የአሕባሹ ቁንጮ በክፉ ካነሳቸው ሶሐቦች በበለጠ ሰይድ ቁጥብ ብዙ ሶሐቦችን በመጥፎ አላንቋሸሻቸውምን? በኒፋቅስ አልወነጀላቸውምን?
5. ዐብደላህ አልሀረሪ ከሚፈፅመው በላይ ሰይድ ቁጥብ በጅምላ አያከፍርምን?
6. ልክ እንደ ዐብደላህ አልሀረሪ ሰይድ ቁጥብስ የአላህን ከዐርሹ በላይ መሆን አያስተባብልምን?
(በሶሐቦች ላይ የሰነዘራቸውን ሰቅጣጭ ቃላት፣ ኡማውን በጅምላ ያከፈረበትን እና ሌሎችም ከባባድ የዐቂዳ ክፍተቶች በተመለከተ “የኢኽዋን ምሽጎችን ማንኮታኮት ክፍል ሶስትን” በዚህ ሊንክ ገብተው ያንብቡ፡፡http://bit.ly/1NOH55F )
ኢኽዋኖች ሆይ! እውነት የሙስሊሙ ዐቂዳ እንዳይበከል ከተጨነቃችሁ፣ እውነት የአሕባሾች ጠማማ አካሄድ ካሰጋችሁ ለምን አሕባሾች ላይ የምታዩትን ጥመት የራሳችሁ ሰዎች ላይ ስታዩት አታስጠነቅቁም?
ምናልባት “ኢኽዋኖቹ ውጭ ነው ያሉት እኛ ምን አገባን ሀገራችን ስላለው አደጋ ነው የምናወራው” እንዳትሉ ይሰሄው ችግሩ በሀገራችንም በሰፊው አለ፡፡ በዚያ ላይ ከካፊሮች በከረጀችሁት እስታይ የሙት አመቱን የምታከብሩለት ሰይድ ቁጥብ ኪታቦቹ በየዩኒቨርሲቲው ሲከፋፈሉ ነበር፡፡ ይሄው የሱ ጥመቶች ስለተጋለጡ ብቻ በርካቶች ሲንዘረዘሩ እያየን ነው፡፡ በርካቶች በየመድረኩ፣ በየፌስቡኩ ሲያስተዋውቁትም እያየን ነው፡፡
ሌላውን ተውትና አፋችሁን ከፍታችሁ በአፍሪካ ቲቪ ከምትከታተሏቸው “ዱዐቶች” ውስጥ በግልፅ የአላህን ከዐርሹ በላይ መሆን የማይቀበል፣ አሕባሾችን በዐቂዳ ጉዳይ እንደማይቃወማቸው የሚናገር አለ፡፡ በሀገራችን በሰፊው የሚገኙት አሽዐርዮች አቋምም እራሱ የአሕባሾች አቋም ነው፡፡ የሱፍዮቹም አቋም የታወቀ ነው “አላህ ከሁሉም ቦታ ይገኛል” ነው የሚሉት፡፡ አሕባሽ ላይ የሚገኘው ጥፋት ይሄው እነዚህም ላይ አለ፡፡ ግና ለተመሳሳይ ጥፋት ተመሳሳይ አቋም አታንፀባርቁም፡፡ ኢኽዋኖች ሆይ! ታዲያ አሕባሾችን የምትቃወሟቸው በምናቸው ነው? ይሄውና ከኢኽዋን አመራሮች አንዱ የሆነው ሰዒድ ሐዋ የአሕባሾችን ብልሹ ዐቂዳ ቃል በቃል ሲያሰፍረው ተመልከቱ፡-
“አላህ ዐዘ ወጀል አለም ውስጥም አይደለም፣ #ከአለም_ውጭም_አይደለም፡፡ ከቀኝም አይደለም፣ ከግራም አይደለም፡፡ #ከላይም_አይደለም፣ ከታችም አይደለም፡፡ ከፊትም አይደለም፣ ከኋላም አይደለም፡፡ ከአለም ጋር ተያይዞም አይደለም፣ #ተነጣጥሎም_አይደለም” ይላል፡፡ [ጀውለቱን ፊልፊቅሀይን፡ 55]
ኢና ሊላሂ ወኢና ኢለይሂ ራጂዑን!!!!
በኢኽዋኖች ደጋሚ ምላስ ለተሸወዳችሁ ነገር ግን ማስተዋል ለምትችሉ ብቻ! (“የምገስፃችሁ ባንዲት ነገር ብቻ ነው፡፡ (እርሷም) ሁለት ሁለት፣ አንድ አንድም ኾናችሁ ለአላህ እንድትነሱ ከዚያም እንድታስተነትኑ ነው” በላቸው፡፡) [ሰበእ፡ 46] እስኪ በንፁህ ልቦናችሁ መልሱ፡፡ ይሄ ከላይ የተሰፈረው ከኢኽዋን ቁንጮዎች አንዱ የሆነው የሰዒድ ሐዋ ንግግር ከአሕባሾቹ ዐቂዳ በምንድን ነው የሚለየው? ለራሳችሁ ታማኝ ሁኑ፡፡ ልባችሁ የሚረጋጋበት የሆነ መልስም ለራሳችሁ ስጡ፡፡ አድበስብሳችሁ እራሳችሁን እንዳትሸውዱ፡፡ የአሕባሾቹን ጥፋት ስትሰሙ የተሰማችሁ አይነት ስሜት ተሰምቷችኋልን? ሚዛናዊ የሆነ አቋምስ ወስዳችኋልን? ወላሂ ከነዚህ ሰዎች ብዙዎቹ ለቡድናዊ አላማ የሚተጉ የዲን ነጋዴዎች ናቸው፡፡ ሐቅን ቢፈልጉ ኖሮ በተመሳሳይ ጥፋት እየለዩ ባላስጠነቀቁ፣ እየለዩም ባልተከላከሉ ነበር፡፡ ይሄ ጥፋታቸው አልበቃ ብሎ አጋጣሚዎችን እየጠበቁ ወደ ተውሒድ የሚጣሩ ሰዎችን ለማሳጣት መሞከራቸው ነው የሚደንቀው፡፡
ቀድሞ ነገር የኢኽዋኖች መንገድ ትኩረት ፖለቲካ ወይም ቡድናዊ ጥቅም እንጂ የትኛውንም የዐቂዳ ብክለት ለማረቅ አይደለም፡፡ በዚህ ላይ በርካታ ዑለማዎች ስለተናገሩ ሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ፡፡ ለጊዜው ግን የቡድኑ መስራች ሐሰን አልበና እራሱ የተናገረውን ላስቀምጥ፡
“የኢኽዋን እንቅስቃሴ ከዐቂዳዎች የየትኛውም ዐቂዳ ወይም ከሃይማኖቶች የየትኛውም ሃይማኖት ወይም ከአንጃዎች የየትኛውም አንጃ ተፃራሪ አይደለም፡፡” [ቃፊለቱልኢኽዋን ሊስሲሲ፡ 1/21]
እውነት ተናገረ፡፡ ለዚህም ነው ከምስረታው ጀምሮ ኢኽዋነልሙስሊሚን ዛሬም ድረስ በውስጡ ክርስቲያኖች የሚገኙበት፡፡ ለዚህም ነው በጥፋታቸው አሕባሽን ከሚያስከነዱት ራፊዳ (ሺዓዎች) ጋር ዛሬም ድረስ ጥብቅ ቁርኝት የሚያደርጉት፡፡ ለዚህም ነው የኸዋሪጅ ንኡስ ክፍል ከሆኑት ኢባዲያዎች ጋር ህብረት የሚሰሩት፡፡ ለጥቆማ ያክል የዐለም ዑለማ ማህበር ሊቀመንበር ተብየው ዩሱፍ አልቀርዷዊ ከምክትሎቹ አንዱ ሺዐ ሲሆን አንዱ ደግሞ ኻሪጂዩ አሕመድ አልኸሊሊ ነው፡፡ ሶስተኛው የኢኽዋን ሙርሺድ የነበረው ዑመር አትቲልሚሳኒ “ኢኽዋኖች ከሺዐህ አመራሮች ጋር ያላቸው ግንኙነት ተቋርጦ አያውቅም” ይላል፡፡ “ታዲያ ምን ችግር አለው? ከጥመታቸው እንዲመለሱ ብንቀርባቸው” ይባል ይሆናል፡፡ ቢሆን በታደልነው፣ ትስስራቸው እነሱን ለማረቅ እንዳልሆነ እራሱ እንዲህ በማለት ይነግረናል፡- “ኢኽዋኖች ይህን ሁሉ የሚያደርጉት ሺዐዎችን መዝሀባቸውን እንዲተው ለማድረግ አይደለም፡፡”
ኢን ሻአላህ ይቀጥላል፡፡
(ኢብኑ ሙነወር፣ ነሀሴ 28/2007)

Post a Comment

1 Comments

  1. ጀዛከላሁ ኸይረን ወንድም ኢብኑ ሙነወር ከስሜት ነፃ ለሆኑት በጣም ትልቅ ትምህርት ነው።

    ReplyDelete