Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ሱንዮች ሆይ! በሃቅ ላይ ጽኑ

Selsebil Zumekan's photo.
بسم الله الرحمن الرحيم
الحمد لله الذي أرسل رسوله بالهدى ودين الحق ليظهره على الدين كله وكفى بالله شهيدا وأشهد أن لا اله الا الله إقرارا به وتوحيدا وأشهد أن محمدا عبده ورسوله صلى الله عليه وعلى آله وصحبه وسلم تسليما مزيدا
أما بعد:
ኢማም አልበርበሃሪ እንዳሉት “ሱና ማለት ኢስላም ነው፤ ኢስላም ማለት ሱና ነው” ስለዚህ ሱኒይ ማለት የነቢዩን (ሰለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም) መመሪያ ብቻ በመከተልና ቢድዓን በመራቅ እስልምናን የሚተገብር ንፁህ ሙስሊም ማለት ነው::
የሰው ልጆች አእምሯቸውን ብቻ በመመርኮዝ አላህ የሚወደውን ሊሰሩና ወደርሱ የሚያደርሰውን ጎዳና ሊደርሱበት ስለማይችሉ አላህ በራህመቱ ከርሱጋ የሚያተሳስሩ እሱን በስሞቹና ባህሪያቱ የሚያሳውቁ ነቢያትን አካታትሎ ልኳል:: ይህም ለሰዎች ከተዋለላቸው ፀጋዎች ሁሉ ከፍተኛውና ጌታችንም ዘወትር ሊመሰገንበት የሚገባ ችሮታው ነው:: ወሊላሂል ሀምዱ ወልሚናህ::
አላህ በመደምደሚያው ነቢይ አማካኝነት ዲነል ኢስላምን ከሞላና በሁለቱም ዓለም ለሰው ልጆች አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን በሙሉ ካሟላ በኋላ እንዲህ ሲል ውለታውን አስታውሷል፦
الْيَوْمَ أَكْمَلْتُ لَكُمْ دِينَكُمْ وَأَتْمَمْتُ عَلَيْكُمْ نِعْمَتِي وَرَضِيتُ لَكُمُ الْإِسْلَامَ دِينًا
“ዛሬ ሃይማኖታችሁን ለናንተ ሞላሁላችሁ፡፡ ጸጋዬንም በናንተ ላይ ፈጸምኩ፡፡ ለእናንተም ኢስላምን ከሃይማኖት በኩል ወደድኩ::” (አልማ ኢዳህ 3)
ኢማም ማሊክ እንዳሉት “የዚህን ኡማ መጨረሻ የሚያበጀው መጀመሪያውን ያበጀው ብቻ ነው” “የዛኔ ዲን ያልሆነ ዛሬ ዲን ሊሆን አይችልም”
በመሆኑም እስልምናን አላህ በሚፈልገው መልኩ ሊተገብር የፈለገ ማንኛውም ሰው የነቢያችንን (ሰለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም) ሱና የሳቸውን መመሪያ ከመከተል ውጭ ሌላ ምንም አማራጭ የለውም::
ከላይ እንደጠቀስኩት ሱና ላይ መሆን የሰው ልጆች ከታደሏቸው ስጦታዎች ሁሉ ከፍተኛውና ምንም አምሳያ የሌለው እድል ነው:: ምክንያቱም ነቢያችን (ሰለሏሁ ዐለይሂ ወሰለም) “አላህ ዱንያን ለሚወደውም ለማይወደውም ይሰጣል፤ ዲንን ግን ለሚወደው እንጂ አይሰጥም” ብለዋል:: ይህንን ሀዲስ ከላይ ካሳለፍነው የኢማም አልበርበሃሪይ ንግግር ጋር አጣምረን ስናስተውል ሱናን መከተል እጅግ በጣም ትልቅ እድል እንደሆነ በቀላሉ መረዳት እንችላለን::
ስለሆነም የዚህ ታላቅ እድል ባለቤት የሆነ ሱኒይ በተቸረው እድል አላህን ዘወትር ሊያመሰግንና ባለበት ሀቅ ላይ እጅጉን ፅኑ ሊሆን ግድ ይለዋል::
በተለይ ባለንበት ዘመን በርካታ ፊትናዎች እየተከታተሉና አንዳንድ የሱና አፍቃሪ የነበሩትም ሳይቀሩ እየተንገዳገዱ የሚስተዋልበት ሁኔታ ስላለ ከየትኛውም ጊዜ በበለጠ ፅናት ሊኖረንና የጌታችንን ጥበቃ ልንማፀን ይገባናል::
ዑለማዎቻችን ከቁርአንና ሀዲስ መዘው ካስቀመጧቸው የፅናት ሰበቦች መካከል ዒልም አንደኛውና ወሳኙ ነው:: የቁርአንና ሀዲስ እውቀታችንን መጨመርና የችግሮቻችንን መፍትሄዎች ከቅዱስ መፅሀፋችን መፈለግ ትክክለኛና ፈጣን ፈውስ የሚያስከትል መድሃኒት ነው::
እንዲሁም የሱና ዑለማዎችን አማካሪ ማድረግና ለሚገጥሙን አጋጣሚዎች ሁሉ ከቁርአንና ሀዲስ መፍትሄ እንዲፈልጉልን በአክብሮት መጠየቅ ጌታችን ያመላከተን የመድህን መንገድ ነው::
አላህ እንዲህ ብሏል፦
وَإِذَا جَاءَهُمْ أَمْرٌ مِّنَ الْأَمْنِ أَوِ الْخَوْفِ أَذَاعُوا بِهِ ۖ وَلَوْ رَدُّوهُ إِلَى الرَّسُولِ وَإِلَىٰ أُولِي الْأَمْرِ مِنْهُمْ لَعَلِمَهُ الَّذِينَ يَسْتَنبِطُونَهُ مِنْهُمْ
“ከጸጥታ ወይም ከፍርሃት አንዳች (ወሬ) በመጣላቸውም ጊዜ እርሱን ያጋንናሉ፡፡ ወደ መልክተኛውና ከእነርሱ ወደ ትዕዛዙ ባለቤቶች (ወደ ዐዋቂዎቹ) በመለሱት ኖሮ እነዚያ ከእነርሱ (ነገሩን) የሚያውጣጡት ባወቁት ነበር”
ይህ ሆኖ ሳለ ግን ፊትና ብቅ ባለ ቁጥር ሰዎች ወደ ዑለማዎች እንዳይመለሱና በፈትዋቸው እንዳይጓዙ እንቅፋት የሚሆኑ ሸያጢኖች እንደሚበራከቱም መዘንጋት የለበትም:: ተጨባጭ ምሳሌ ለመስጠት ያህል የሰውን ደም ያላግባብ የሚያፈሱ እርኩስ ኸዋሪጆች (ዳዒሽ ወይም isis) ብቅ ካሉበት ጊዜ ጀምሮ የሱና ምሁሮች ማስጠንቀቂያ ሲሰጡ ቆይተው ኖረው ባለንበት ወቅት በየ ሶሻል ሚዲያው የዑለማዎች ምክር ከምንም እንዳይቆጠር እንዲያውም በጥርጣሬ እንዲታይ በአንፃሩ ደግሞ የእርኩሶች ውዳቂ ስራ እንደ ጀግንነትና እስካሁን እንዳልተሰራ ትልቅ ቅዱስ ጅሃድ አድርገው የሚሰብኩ “የጀሐነም በር ላይ ተጣሪዎች” ተበራክተው እየተመለከትን ነው::
ይህ የሚያሳየው ከየትኛውም ጊዜ በበለጠ በፈተናዎች እንደተከበብንና ከዑለማዎቻችን ጋር በጠንካራ ገመድ ካልተሳሰርን የመጥፊያችን ጊዜ ቅርብ እንደሆነ ነው:: አላህ እኔንም እናንተንም ከጥፋት ይጠብቀን::
ሌላው የፅናት ሰበብ ከሙብተዲዖችና ከተለያዩ የሱና ተፃራሪ የሆኑ አይዲዮሎጂ አራማጆች ጋር ያለንን ግንኙነት በሸሪዓዊ መርሆዎች ማጠርና በተለይ አጉል ክርክሮችን እርግፍ አድርጎ መተው ነው::
ኢማን አህመድ እንዲህ ይላሉ፦
"وترك الخصومات والجلوس مع أصحاب الأهواء"
“ክርክሮችን መተው ከስሜት ባለቤቶች ጋር ከመቀማመጥ መታቀብ (ከሱና መሰረቶች አንዱ ነው::)” (ኡሱሉ ሱና)
ከሙብተዲዖች ጋር የሚደረጉ ክርክሮች በእውቀት በጥበብና በጥንቃቄ ካልተለጎሙ ከጥቅማቸው ጉዳታቸው አመዛኝ ስለሚሆንና ተከራካሪውን ወይም ተከታታዮችን ፊትና ውስጥ ሊከት ስለሚችል እንዲሁ ልቅ የሆኑና ለማንኛውም ሰው ክፍት የተደረጉ አይደሉም:: ይህንን የሱና መሰረት በሚገባ የሚያውቁ ብዙሃን ወንድሞች ግን ብዙ ጊዜ ሳይተገብሩት ሲቀሩ የሚስተዋል ነው:: አላህን በእውቀታችን ተጠቃሚዎች ያድርገን::
ሰበቦችን ከማስገኘት በተጨማሪ ዋናውና በፍፁም ሊዘነጋ የማይገባው የፅናት ሰበብ ደግሞ ዱዓ ነው::
አላህ እንዲህ ይላል፦
ظَهَرَ الْفَسَادُ فِي الْبَرِّ وَالْبَحْرِ بِمَا كَسَبَتْ أَيْدِي النَّاسِ لِيُذِيقَهُم بَعْضَ الَّذِي عَمِلُوا لَعَلَّهُمْ يَرْجِعُونَ [٣٠:٤١]
“የሰዎች እጆች በሠሩት ኃጢኣት ምክንያት የዚያን የሠሩትን ከፊሉን ያቀምሳቸው ዘንድ መከራው በየብስና በባሕር ተሰራጨ፡፡ እነርሱ ሊመለሱ ይከጀላልና::” (ሩም 41)
በዚህ አንቀፅ ላይ በግልፅ እንደተነገረው ምድር ላይ ጥፋት የሚመጣው በሰዎች ኃጢአት ምክንያት እንደሆነና እንዲሁም ወደ አላህ እንድንዞርም ተፈልጎበት ነውና ወደርሱ ከምንዞርባቸው ዋነኛ መገለጫ የሆነውን ዱዓ ልናበዛ ይገባል::
نسأل الله أن يجنبنا الفتن ما ظهر منها وما بطن وصل اللهم وسلم وبارك على نبينا محمد وعلى آله وصحبه وسلم والسلام عليكم ورحمة الله وبركاته