Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ሊስተካከል የሚገባው ግንዛቤ ሚስት የቤቷ ውስጥ ስራ ይመለከታታልን ?

ተንቢሀት - ሙስሊም ሴቶችን የተመለከቱ ህግጋት

~° ሊስተካከል የሚገባው ግንዛቤ °~

የተንቢሃት ሳምንታዊ መልእክት ቁ• 4

ሚስት የቤቷ ውስጥ ስራ
ይመለከታታልን ?

[ ከዚህ ቀደም በተንቢሃት ፔጅ ላይ ቀርቦ የነበረውን የቪዲዮ መልእክት ብዙሃኑ ይረዱት ዘንድ ወደ አማርኛ እንዲመለስ ተደርጓል። ያንብቡት ]

አላህ ይጠብቃቸውና ለሸይኽ ሱለይማን ቢን ሰሊመላህ አልሩሀይሊ የትዳር አጋሮች መተጋገዝን በተመለከተ ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር:-

ጥያቄ
•••••••
# ሚስት በባሏ ቤት ምግብ ማብሰል፣ ልብስ ማጠብና ሌሎችም ግዴታዋ አይደለም መባሉ ትክክል ነውን ?

# ለባሏ ማድረግ የሚገባት እንክብካቤም ከሱ ጋር በመልካም ለመኗኗር ስትል ብቻ ነውን ?

# የቤት ውስጥ ስራዎችን አልሰራም በማለት ባሏን ባለመታዘዟስ ኃጢኣተኛ ትሆናለችን ?

ጀዛኩሙላሁ ኸይረን።

ምላሻቸው:
````````````
አልሃምዱሊላህ በጥያቄው ላይ የተወሳው አይነት አባባል አንዳንድ ሊቃውንት ብለውታል።

ነገር ግን (ሌሎች ሊቃውንት የተናገሩት ሚዛን በመድፋቱ ይኸኛው አባባል) ተበላጭ ነው።

ይህም ከሁለት ጉዳዮች የተነሳ ነው።

የመጀመርያው ጉዳይ (መረጃ)
•••••••••••••••••••••••••••••••
አላህ አዝዘ ወጀልለ እንዳለው
" وَعَاشِرُوهُنَّ بِالْمَعْرُوفِ "
سورة النساآ: 19

« በመልካምም ተኗኗሯቸው »
አል ኒሳእ: 19

እንዲሁም

" وَلَهُنَّ مِثْلُ الَّذِي عَلَيْهِنَّ بِالْمَعْرُوفِ ،"
سورةالبقرة: 228

« ለእነርሱም (ለሴቶች) የዚያ በእነርሱ ላይ ያለባቸው (ግዳጅ) ብጤ በመልካም አኗኗር (በባሎቻቸው ላይ መብት) አላቸው። »
አልበቀራህ:228

" ኡርፍ (መልካም አኗኗር) " ሲባል ለማለት የተፈለገው በባህሉ በተለምዶ ሙስሊሞች መካከል ያለውን ሸሪኣን የማይጣረስ የአኗኗር ዘይቤ ነው።

ባካባቢዋ ተለምዶ መሰረት ከባሏ ጋር መኗኗርም በሚስት ላይ ግዴታ ይሆናል።

ጥንትም ይሁን አሁን ባለው የሙስሊሞች ባህል መሰረት ሚስት ባሏን ትንከባከባለች (በቤት ውስጥ ስራ ባሏን ታግዛለች)።

በቤቷ ውስጥ እንቅስቃሴዎች በሙሉ ባሏን ለመንከባከብ ትሳተፋለች።

(ካልሆነስ ቤቷን ችላ ብላ)
ኑሮስ እንዴት ያማረ ይሆናል ?

ባሏን ሳትንከባከብ እንዴትስ በመልካም አብሮ መኗኗር ይኖራል ?

አላህ እንዳለው

« በመልካምም ተኗኗሯቸው »

« ለእነርሱም (ለሴቶች) የዚያ በእነርሱ ላይ ያለባቸው (ግዳጅ) ብጤ በመልካም አኗኗር (በባሎቻቸው ላይ መብት) አላቸው። »

የሚሉ አንቀፆች

ሚስት በቤቷ ውስጥ ባለው ጉዳይ ላይ …
★ ከአቅሟ በላይ ጫና ሳይፈጠርባትና

★ ቤቷን እርግፍ ሳታደርግ ስለቤቷ ቸልተኝነት በሌለበት ሁኔታ ፤ በዚህ መሀል በሚዛናዊነት ባሏን መንከባከብ እንዳለባት የሚገልፅ ኣስረጅ ነው።

ከነቢዩ ﷺ ዘመን እስካሁኑ ዘመን ድረስ በሙስሊሞች ባህል መሰረት ሚስት ባሏን ትንከባከባለች።

ሁለተኛው:መረጃ
•••••••••••••••••

ነቢዩ ﷺ ሚስት ባሏን እንድትታዘዝ አዘዋታል።

ይህንንም ጉዳይ ጠንከር በማድረግ ከአቢሁረይራ በተወራልን መሰረት ነቢዩ ﷺ ቀጣዩን ብለዋል።

وعن أبي هريرة عن النبي صلى الله عليه وسلم قال :
{ لو كنت آمرا لأحد أن يسجد لأحد لأمرت المرأة أن تسجد لزوجها }

« አንድ ሰው ለሌላው እንዲሰግድ የማዝ ብሆን ኖሮ ሚስት ለባሏ እንድትሰግድ ባዘዝኩ ነበር ። »

ይህ እንግዲህ በሷ ላይ ግድ የሆነውን የባሏን ሀቅ ክብደት ለመግለፅ ነው።

አንድ ባል በሆነ ጉዳይ ላይ ሚስቱን አዝዞ ካልታዘዘችውና በዚህም ካስቆጣችው የረህማን መላኢካዎች ይቆጡባታል።

ባል እንድትንከባከበው ሲያዛት ልትታዘዘው ይገባታል።

ይህ እንግዲህ ሸሪዓው የወሰነውና አብዛኞቹ ምሁራንም የደገፉትና ትክክለኛውም ነው።

ከዚህ ውስጥ ግን የሚነጠል ጉዳይ አንድ ሁኔታ ይኖራል።

እሱም

★ ያካባቢው ተለምዶ ወይም ባህል ሚስት ባሏን በመካደም የማይታወቅበት ከሆነ ይህ ጉዳይ ይነጠላል።

ምክንያቱም ከባህላቸው ውጭ ስለሆነ ነው።

ለክብራቸው ወይም ባካባቢዋ ተለምዶ ሚስት ባሏን መኻደም ከሌለበት ቤት ወይም ማህበረሰብ የመጣች ሴትም በቤት ውስጥ ስራ ባሏን ከመንከባከብ ግዴታ ውጭ ትሆናለች።

(በፍላጎቷና በመተዛዘን ግን ታደርገዋለች)

* በማስከተል የምለው ነገር…
ስለ ሰዎች ጉዳይ የሚናገር ሰው የጠለቀ ግንዛቤ ሊኖረው ይገባል።

የታወቀው ነገር ሁሉ አይነገርም ።

ከሰዎች ጋር (ስለ ትዳር ህይወታቸው) የሚያወራ ሰው የነዚያን የሚያናግራቸውን ሰዎች ህይወት የሚያሳምር ነገር ሊመርጥ (ሊያጠና) ይገባዋል።

ያ ቤተሰብ በምን መንገድ ስኬታማነት እንደሚሰፍንበት ሊያጠና ግድ ይለዋል ።

ተፈላጊው ጉዳይ ቤተሰባዊ ደስታ መፍጠር ነውና።

# በባልና ሚስት መካከል ደስታ እንዴት ሊገኝ እንደሚችል ማስተዋሉ ሊተኮርበት ይገባል።

አንዳንድ ስለ ዒልም የሚያወሩ ወይም ዓሊምነትን ለማሳየት የሚሞክሩ ግለሰቦች…

ባልሽን መንከባከብ ማገልገል ግዴታሽ አይደለም ብለው ሲናገሩ ትሰማለህ።

በዚህም የተነሳ ባሏ ወደ ቤት መጥቶ ምግብ ፈልጎ ሲጠይቃት እንኳ …

" እኔ እገሌ የሚባል ሸይክ ባልሽን መንከባከብ ግዴታሽ አይደለም ሲል ሰምቼዋለሁ " ትለዋለች።
(ይህን ክስተት አስተውሉ)
ሸሪዓው በባልና ሚስት መካከል እንዲኖር የሚፈልገው ፍቅርና ውዴታ የታለ ? !
በመልካም አብረው መኗኗር የተባለውስ የታለ ? !

ይህ አካሄድ የሸሪዓን ፍላጎት ይጣረሳል። ¹

ስለሆነም ወንድሞቼ ሆይ !
ከፊቅህ (ከጥልቅ ግንዛቤ) አንዱ የምታውቀውን ሁሉ ኣለማሰራጨት ነው።

ማሰራጨት ያለብህ የደንጋጊውን (የህግ አውጪውን) ግብ ወይም ፍላጎት የሚያሳካውን ነው።

አንዳንዱ ሰው የሆነ ነገር ከኪታብ ላይ ሲያነብና ለሱ እንግዳ የሆነ ነገር ሲያይ ከእውቀት ማነስ የተነሳ ወይም ከግንዛቤ እጥረት የተነሳ … ያ እንግዳ የሆነበትን ነገር ወዲያው ለሰዎች ይፋ ያደርጋል …… ያሰራጫል።

ከዚያም ምሁራን እንዲያ ብለዋል ይላል ።

እርግጥ ነው አንዳንድ ኡለማእ እንደዚያ ብለዋል ። ነገር ግን በሰዎች መካከል ፍሬያማ ውጤት አያመጣም።

ሁሌም ለወንድሞቼ የማወሳቸው መጠይቅ ኣለች ።


እሷም አንድ ሰው የሆነ ንግግር ሲናገር ሶስት ጉዳዮችን ማስተዋል ይገባዋል የምትል ናት።

①ኛ - ንግግሩ ሀቅ መሆን አለበት። የግድ ከሸሪዓ ጋር የገጠመ የተስማማ መሆን ይገባዋል።

ሊቃውንት የተናገሩት ሁሉም ወይም የከፊሎቹ ከትክክለኛ ማስረጃ ጋር ይገጥማል ይስማማል ማለት አይደለምና። ²

②ኛ - የተናጋሪው ውስጣዊ ፍላጎት ሀቅን ፈልጎ መሆን ይገባዋል። የአላህን ፊት ፈልገህ የምትናገር መሆን አለበት።

ፍላጎትህ የሴቶችን ልቦና ማግኘት (የነሱን ውዴታ ማትረፍ ድጋፋቸውን ማግኘት እነሱን ማስደሰት) መሆን የለበትም። ³

ሰዎች የማያውቁትን እንግዳ ነገር በመናገር የሰዎችን አድናቆት ለማካበት መሆን የለበትም። ዓላማህ የአላህ ፊት ፍለጋ መሆን ይኖርበታል።

③ኛ - ንግግሩ የሚያሳርፈው ተፅዕኖ ሀቅ (ጠቃሚ) መሆን አለበት።

ሀቅን የሚያፈራ ፣ መልካምን የሚያስፋፋ፣ ወደ ኸይር የሚወስድ መሆን ይገባዋል።

ነገር ግን ይህ ንግግር ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚያመዝን ከሆነ ያንን ንግግር ልትናገረው፣ ልታስተላልፈው አይገባም። ⁴


ሌላው ላብራራላችሁ የሚገባው ጉዳይ:

እናንት ባሎችና ሚስቶች ሆይ !

① የትዳራችሁ መነሻ አቋማችሁ በመልካም አብረው መኖር መሆን ይገባዋል።

② ደስታ ያለበትን ቤት መመስረት መሆንም ይኖርበታል።

③ እርካታ የሰፈነበት (ህይወት ልታደርጉት ይገባል)።

④ በአላህ እምላለሁ……
ቤት (የትዳር ኑሮ) ካልፀና በስተቀር ልብም አይረጋጋም።

√ የኑሮ ስልታችሁ ከአላህ ኪታብና ከመልእክተኛው ﷺ ሱና ካልተገጣጠመና

√ ፍቅራችሁ ካልፀና እንዲሁም

√ በመልካም ሁኔታ አብሮ መኗኗር ካልተገኘ በስተቀር ልብ አትረጋጋም ቤትም አትፀናም።


(እግረ መንገዴን ልጠቁማችሁና የትዳር አጋሮችን የተመለከቱ)
ሁለት የታተሙ መልእክቶችም አሉኝ ። እነርሱም:

" أسباب سعادة الأسر "

« የቤተሰባዊ ደስታ መገኝያ ሰበቦች»

ሌላኛው

" حقوق الزوجين"

« የባልና ሚስት መብቶች»

በቁርኣንና በሱና መረጃዎች ላይ ተመስርቼ ያዘጋጀሁትም ነውና

በነዚህም (መፅሃፍት መልእክት) ለባለ ትዳሮች መልካም ውጤት እንዲገኝበት እከጅላለሁ። ወላሁ አዕለም።
__________

ከተርጓሚው ማብራርያ ↓↓↓↓

¹- በሸሪዓችን በኢስላም በባለ ትዳሮች መካከል እንዲኖር የሚፈለገው

~ ፍቅር፣ መተዛዘን፣ መግባባት፣ መረዳዳት፣ መቻቻል፣ አንዱ ኣንዱን መንከባከብ፣… የመሳሰሉት ናቸው።

በመሆኑም ፍቅርና መግባባትን የሚያጠፋ ተግባርና አስተሳሰብ ሁሉ ውድቅ ነው።

ስለሆነም ብዙውን ግዜ ሚስት የማይንከባከባትን፣ የማይፍጨረጨርላትን ባል እንደማትወደው ሁሉ

ባልም የማትንከባከበውን ፣ ቤቷን ችላ የምትልን ሚስት ሊወዳት አይችልም ።

እንክብካቤ፣ ታዛዥነትና፣ የህይወት ጣጣን መጋራት በራሱ የፍቅር መገለጫም ነው።

የቤት ውስጥ ጣጣን በመሸፈን ባልን መንከባከብ በተመለከተ ላገራችን እንስቶች የሚነገር አዲስ ነገር ብዙም የለም ።

ያደግንበት ፣የወረስነውና ያለንበት ነውና።

ነገር ግን በአንዳንድ ምክር አቀባዮች ያልተጠና ዲስኩር መስመር መልቀቅና ክርክር መግጠም ሳይመጣ መተዋወሱ መልካም ነው በሚል ነው ይህ ርእስ የተተረጎመው።

² - ምሁራን ስለ አንድ ጉዳይ ስለተናገሩት ብቻ ተቀባይነት አይኖረውም ።

ነገር ግን ካለው ኢስላማዊ መረጃ ጋር ይተያይና ከተስማማ የወሰዳል፤ ካልገጠመ ግን ይተዋል።

ይህንንም የኢስላም ሊቃውንት የተስማሙበትና የሚተገብሩትም፣ ኣንዳቸው ያንዳቸውን የሚተራረሙበትም ነውና።

³ - ስለ ሴት ልጅ ተቆርቋሪ መስሎ የሚናገር ሰው ለመብታችን ቆሟል ብለው ሴቶች እንዲያጨበጭቡለት፣ የነሱን ልቦና ለማግኘት፣ ውዴታቸውንና ድጋፋቸውን ለማትረፍ እንዲሁም እነሱን ለማስደሰት በሚል ብቻ ባልሽን የመንከባከብም ሆነ የቤት ውስጥ ሃላፊነት አይጠበቅብሽም ብሎ ማስተማር ወይም ማውራት የተሳሳተ አቋም ነው።

⁴ - ትምህርት ሲሰጥ በተማሪው ወይም በአድመጩ አቅምና ግንዛቤ ልክ መሰጠት አለበት።

ያለውን ነባራዊ ህይወት ያገናዘበና የባሰ ችግር የማያስከትል ሊሆን ይገባል።

ያለዚያ ያደናግርና ይበልጥ ግራ እንዲጋባ ያደርጋል እንጂ መልካም ተፅዕኖ አይኖረውም።
_____________
#ተከታዩን-ሊንክ-በመጫን-ፔጁን-ላይክ(l­ike)-ያድርጉ

www.facebook.com/tenbihat
`````````````````````
12Rabi'e al-awal 1436
abufewzan 03Jan15
••