Header Ads Widget

Ticker

6/recent/ticker-posts

ጥቂት ስለ ምስል ፣ ፎቶ ፣ ስእል ...


بسم الله الرحمن الرحيم
ድሮ ስእል በመሳል ላይ የሚሰማሩት ጥቂቶች ነበሩ፡፡ ዛሬ ግን ከድሮው በተሻለ ምስልን ለማስገኘት ያን ያክል ብቃትም አይጠይቅም፡፡ ዘመናዊ መሳሪያዎችን በመጠቀም ከህፃን እስከ አዋቂ፣ ከገጠሬ እስከ ከተሜው ሁሉም በቀላሉ ምስሎችን ማምረት ይችላል፡፡ የሰራውንም በቀላሉ በማህበራዊ ድረ-ገፆች መልቀቅ ይችላል፡፡
ስእል መሳል በዲናችን የተወገዘ ምግባር ነው፡፡ ኧረ እንዳውም ከከባባድ ወንጀሎች ውስጥ የሚመደብ ነው፡፡ ይህን ከሚያመላክቱ ማስረጃዎች ውስጥ ጥቂቶቹን ለማየት እንሞክር፡፡ ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እንዲህ ይላሉ፡-
1. “ከሰው ሁሉ ቅጣት የሚበረታባቸው ሰዎች ሰአሊዎች ናቸው፡፡” (ቡኻሪና ሙስሊም)
2. “የቂያማ ቀን የሚያዩ ሁለት አይኖች፣ የሚሰሙ ሁለት ጆሮዎች እና የሚናገር ምላስ ያለው አንገት ከእሳት ውስት ይወጣና እንዲህ ይላል፡ እኔ በሶስት ሰዎች ላይ ተወክያለሁ፡፡ በእያንዳንዱ አረመኔ አንባገነን ላይ፤ በእያንዳንዱ ከአላህ ጋር ሌላን አምላክ በተጣራ እና በሰአሊዎች ላይ!!” (ቲርሚዚ)
3. ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ሰኣሊን ተራግመዋል፡፡ (ቡኻሪ)
ሱብሓነላህ! እነዚህ ሐዲሦች ምንኛ አስፈሪ መልእክት ነው የያዙት!! ጌታዬ ሆይ ከአሳማሚውና አስፈሪው ቅጣትህ እና ከነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እርግማን አንተው ጠብቀን፡፡ ምስል ያለበት ቤት መላእክት አይገባም!! ይህን አስመልክተው ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እንዲህ ይላሉ፡-
1. “ምስሎች ካሉበት ቤት ውስጥ መላእክት አይገቡም፡፡” (ቡኻሪና ሙስሊም)
2. “ውሻና ምስል ካለበት ቤት ውስጥ መላእክት አይገቡም፡፡” (ቡኻሪና ሙስሊም)
ልብ ይበሉ፡-1
የተከለከለው የምስል አይነት አንዳንዶች እንደሚያስቡት የሚዳሰስ የሚጨበጥ ጥላ ያለው ብቻ አይደለም፡፡ የቅብ ወይም የቀለም ስእሎችም ከዚሁ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ለዚህም ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ስእል ያለበት መጋረጃ ሲያዩ ተቆጥተው ማስወገዳቸው ዋቢ መሆን ይችላል፡፡
ልብ ይበሉ፡- 2
ምስል በየትኛውም መንገድ ቢሰራ ምስል ነው፡፡ በየትኛውም መንገድ ቢገኝም ውግዝ ነው፡፡ “ሰአሊ ሁሉ የእሳት ነው” የሚለው የነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ንግግር ጠቅላይ መልእክት ነው፡፡ ጥቅል ህግ ደግሞ ያለ ማስረጃ አይገደብም፡፡ “አይ በዚህ ጠቅላይ ህግ ውስጥ የማይካተቱ ነገሮች አሉ” የሚል ካለ ጠንካራና የማያሻማ ቁርኣናዊ ወይም ሐዲሣዊ ማስረጃ ሊጠቅስ የግድ ይለዋል፡፡
ልብ ይበሉ፡- 3
ግልፅና የማያሻሙ አስፈሪ የነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ሐዲሶች እየተጠቀሱ ሳለ በተቃራኒው ፍፁም ያልሆኑ ሰዎችን አባባል መጥቀስ አደብ አይደለም፡፡ ሐቅ ፈላጊ የሆነ ሰው ወሕይን በረእይ አይዳፈርም፡፡ ሰማያዊ መልእክትን በግለሰባዊ ንግግር ወይም ተግባር አያፈርስም፡፡ ሌላው ቀርቶ ለምን ተናጋሪው ሶሐባ አይሆንም!! ኢብኑ ዐባስ ረዲየላሁ ዐንሁ፡ “ከሰማይ ድንጋይ ሊዘንብባችሁ ይቀርባል!! የአላህ መልእክተኛ እንዲህ አሉ እላችኋለሁ እናንተ አቡ በክር እንዲህ ብሎ ዑመር እንዲህ ብሎ ትላላችሁ” በማለት አስፈሪ ነገር ይናገራሉ፡፡ አስተውሉ! ሐዲሥ እየተጠቀሰ አቡ በክርንና ዑመርን በተቃራኒው ማጣቀስ እንዲህ ካስባለ ከነሱ እጅግ ያነሱ አካላትን ማጣቀስስ ምን ሊባል ነው? ስለዚህ ለማንም ንግግር ብለን የነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ሐዲሥ ልንጥል አይገባም፡፡ “የአላህ መልእክተኛን ሐዲሥ የመለሰ እሱ የጥፋት አፋፍ ላይ ነው” ይላሉ አልኢማም አሕመድ፡፡
ልብ ይበሉ፡- 4
- ፎቶን የሚፈቅዱ ዑለማዎች እራሳቸው የሚከለክሉባቸውም ብዙ ፈትዋዎች ስላሏቸው ሚዛን የሚደፋውን ሳንፈትሽ ከስሜታችን ጋር የሚሄደውን ብቻ እየመረጥን አንውሰድ፡፡
- የሚፈቅዱት እራሳቸው ለማስታወሻና ለመዝናኛ መጠቀምን፣ ማስቀመጥን አልፈቀዱም፡፡ የማወራው ስለሱና ዑለማዎች ብቻ ነው፡፡
- በዚያ ላይ ደግሞ የዑለማ ንግግር ማስረጃ የሚፈልግ እንጂ በራሱ ማስረጃ አይደለም፡፡ ማስረጃ ያለው በቁርኣንና በሐዲሥ ላይ ነው፡፡ ያሉት ማስረጃዎች ደግሞ አስፈሪና የማያሻሙ ናቸው፡፡
ልብ ይበሉ ፡- 5
ምስል መሳል የተከለከለበት አንዱ ምክኒያት ለባእድ አምልኮ ስለሚያሸጋግር ነው፡፡ ይህን ምክኒያት ብቻ ነጥሎ በማውጣት “የኛ ከዚህ ጋር የሚገናኝ ስላልሆነ ችግር የለውም” የሚሉ አሉ፡፡ ነገር ግን ምስል የተከለከለበት ምክኒያት ይሄ ብቻ አይደለም፡፡ ለምሳሌ ፈጣሪ እንደሚፈጥረው ማመሳሰል መኖሩ አንድ ምክኒያት ነው፡፡ ለዚህም የሚከተሉት ሐዲሦች ማስረጃ ይሆናሉ፡-
1. “አሸናፊና የላቀው አላህ እንዲህ ብላል፡ እንደኔ መፍጠር ሊፈጥር እንደሞከረ ሰው ማን በዳይ አለ?! (ከቻሉ) ቅንጣትን ይፍጠሩ፡፡ የገብስ ፍሬን ይፍጠሩ፡፡” (ቡኻሪና ሙስሊም)
2. “እነዚያ ምስሎችን የሚሰሩ ሰዎች በቂያማ ቀን ይቀጣሉ፡፡ የፈጠራችሁትን ህይወት ዝሩበት! ይባላሉ፡፡” (ቡኻሪና ሙስሊም)
3. “ዱንያ ላይ ምስልን የሰራ የቂያማ ቀን ሩሕ እንዲነፋበት ይገደዳል፡፡ የሚነፋ ደግሞ አይደለም፡፡” (ቡኻሪና ሙስሊም)
4. “ሰአሊ ሁሉ የእሳት ነው፡፡ በእያንዳንዱ በሳላት ምስል ነፍስ ይደረግና ጀሀነም ውስጥ ትቀጣዋለች፡፡” (ቡኻሪና ሙስሊም)
ስለዚህ “እኔ ማመሳሰልን አስቤበት አይደለም” ማለት አያዋጣም፡፡ ምስሉን ማስገኘቱ በራሱ ማመሳሰል ነውና፡፡
ፎቶ የሚፈቅዱ ሰዎች ከማይጨበጡ ፍልስፍናዎቻቸው በተጨማሪ በዋናነት የሚያጣቅሱት ሸይኽ ኢብኑ ዑሠይሚንን ነው ረሒመሁላህ፡፡ ሸይኹ ግን “ማመሳሰል ነው ለማለት ያን አስቦ መስራቱ መስፈርት አይደለም፡፡ እናም ማመሳሰሉ እስከተገኘ ድረስ ብይኑም ተከትሎት ይረጋገጣል” ይላሉ፡፡
ልብ ይበሉ፡-6
አንገብጋቢ ለሆኑ ጉዳዮች ምስልን መጠቀም እንደሚቻል ዑለማዎች ይናገራሉ፡፡ ይሄ ደግሞ “ችግሮች የተከለከሉ ነገሮች ያስፈቅዳሉ” ከሚለው ሸሪዐዊ መርህ የተወሰደና ቁርኣናዊም ሐዲሣዊም መነሻ ያለው ህግ ነው፡፡ ልክ አማራጭ ያጣ ሰው በክት መብላት እንደሚችለው ማለት ነው፡፡ በዚህም መሰረት ለተለያዩ አንገብጋቢ ማስረጃዎች ለምሳሌ፡- መታወቂያ፣ ፓስፖርት፣ መንጃ ፍቃድ፣ የመኖሪያ ፍቃድ፣ የአፋልጉኝ ማስታወቂያ፣ አጥፊዎችን ለማደን፣ ለማስተማርና ለመሳሰሉት መጠቀም ይቻላል ማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ ግን ለችግሩ የሚያስፈልገውን ያክል ብቻ ነው እንድንጠቀም የሚፈቀደው፡፡
ልብ ይበሉ፡- 7
ወንዶች ሆይ! ክልከላው እኮ ወንዱንም ይመለከታል፡፡ ከሴቶች ፎቶ ስር እየተከተልን “አላህን ፍሩ” የምንል ወንዶች ማስታወሳችን ጥሩ ሆኖ ሳለ ነገር ግን እራሳችንንም ልንረሳ አይገባንም፡፡ እህቶቻችንን እንደምናስታውሰው እራሳችንንም ወንድሞቻችንንም እናስታውስ፡፡ እርግጥ ነው ተያያዥ መዘዝ ከመከተሉ አንፃር ካየነው የጥፋቱ መጠን ሊለያይ ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን ወንዱ ይቅር የተባለ እስከሚመስል ዝምታን ባንመርጥ መልካም ነው፡፡ ማህበራዊ ድረ-ገፆች ላይ “አላህን ፍሩ” በማለት ፋንታ “ዋው” “ዊው” እያሉ ለጥፋት ሞራል የምንሰጥ ሁሉ የጥፋቱ ተጋሪዎች እንደምንሆን አንርሳ፡፡
ልብ ይበሉ፡- 8
ምስል አይተን ሳናበላሽ እንዳናልፍ ነብያዊ አደራ ተጥሎብናል፡፡ (አሕካሙል ጀናኢዝ፡ 207) ስለዚህ የቻለ ሰው ፊትና በማይፈጥር መልኩ ምስሎችን የማስወገድ አሃላፊነት አለበት፡፡ ይህ ካልሆነ ግን በምላስ ማስጠንቀቅ፡፡ ይህም ካልሆነ በልብ መጥላት ይጠበቅብናል፡፡ ይህን ድንበር አልፈን ከጥፋቱ ከወደቅን ለጥፋት ልንሟገት፣ ለአጥፊዎች ጠበቃ ልንሆን፣ ለጥፋታችን ሸሪአዊ ሽፋን ልንፈልግ አይገባም፡፡ ይልቁንም ጥፋታችንን ማመን የተሻለ ምርጫ ነው፡፡ አላህ እሱን በመፍራት ላይ ያግዘን፡፡
**
ስለዚህ በማህበራዊ ድረ-ገፆች ፎቷችሁን እየለቀቃችሁ የፊትና ሰበብ የምትሆኑ ወገኖች ሆይ! ፎቶ በመፅሄት የምታወጡ የኮሌጅና የዩኒቨርሲቲ ተመራቂ ተማሪዎች ሆይ አላህን ፍሩ፡፡ እዚህ ግባ ለማይባል የማይጨበጥ ቅፅበታዊ ደስታ ብላችሁ ከአላህ ጋር አትጣሉ፡፡ ወወላሂ ለመፅሄት የተሰበሰቡ ፎቶዎችን መፅሄቱ ላይ አውጥተው ሲመለሱ ቆንጆ ቆንጆ የሚሏቸውን ሴቶች ፎቶ ለማስቀረት ሲመርጡ የነበሩ ወንዶችን በአይኔ አይቻለሁ፡፡ ፌስቡክም ላይ የሴቶችን ፎቶ ግራፍ ለእኩይ ምግባር የሚያውሉ ወንዶችን እየተመለከትን ነው፡፡
አላህ የመልእክተኛውን ትእዛዝ የምናከብር፣ ክልከላቸውንመ የምንርቅ ያድርገን፡፡

وصلى الله على نبينا محمد وعلى آله وصحبه وسلم

Ibnu Munewor